በአዲስ አበባ የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ በተለይ በዚህ ሳምንት ተባብሶ መቀጠሉ የአዲስአበባ ነዋሪዎችን እያበሳጨ ነው፡፡

ጥቅምት (ሠላሳ) ቀን ፳፻፯ / ኢሳት ዜና :-‹በተለይ ባሳለፍነው አንድ ሳምንት ጊዜያት ውስጥ መቆራረጡ በወሳኝ ሰዓታት ጭምር ማለትም በምሽት እና በጠዋቱ ጊዜያት ተጠናክሮ መቀጠሉን የገለጹት ነዋሪዎች በዚህ ምክንያት ለከፍተኛ ኪሳራና ወጪ እየተዳረጉ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ባለስልጣናት «የኃይል እጥረት የለም፣ እንዲያውም ተርፎን ለጎረቤት ሀገራት ኤክስፖርት እያደረግን ነው» በሚሉበት በዚህ ወቅት በተለይ የአፍሪካ ርዕሰ መዲና መሆንዋ በሚነገርላት አዲስአበባ ከተማ በቀን በአማካይ እስከ ሶስት ጊዜ ያህል በተደጋጋሚ ኤሌክትሪክ የሚቆራረጥበት ምክንያት ጨርሶ

ሊገባቸው እንዳልቻለ አስረድተዋል፡፡ ነዋሪዎቹ በቤት ውስጥ እንጀራ ለመጋገር ሲዘጋጁ መብራት እንደሚጠፋ ቆይቶ ሲመጣ እህሉ ለብልሽት እንደሚዳረግባቸው እንዲሁም በወቅቱ በኤሌክትሪክ አብስለው ለመመገብ አለመቻላቸው ተናግረዋል፡፡ አንድ ስሙን መጥቀስ ያልፈለገ ወንደላጤ ወጪ ለመቆጠብ በብዛት

ቤት ውስጥ አብስሎ እንደሚመገብ ጠቅሶ ከቅርብ ሳምንታት ወዲህ ግን መብራት በተደጋጋሚ ስለማይኖር በቋሚነት በሆቴል ለመመገብ መገደዱንና ይህ ደግሞ ከአቅም በላይ ወጪ እንዳስከተለበት በምሬት ተናግሮአል፡፡ አንድ የአራት ልጆች አባት እንደሆኑ የተናገሩ ነዋሪ በበኩላቸው  በቀን እስከአራት ጊዜ መብራት መጥፋቱን

መታዘባቸውን አውስተው መብራት በሚጠፋበት ወቅት ማታ ማታ ልጆች በጊዜ ስለሚተኙ የቤት ስራ እንኩዋን መስራት አለመቻላቸውን አስረድተዋል፡፡

የኤሌክትሪክ ሃይል በሚቆራረጥበት ጊዜ የሞባይልና የኢንተርኔት አገልግሎትም የሚታወክ ሲሆን አግልግሎት ሰጪ ተቁዋማት ማለትም ባንኮች፣ አየር መንገድ፣ ካፌና ሬስቶራንቶችን የመሳሰሉት ድርጅቶች ስራቸው እንደሚስተጉጎል ዘጋቢያችን ካሰባሰበው መረጃ ለመረዳት ተችሎአል፡፡

የውሃ፣መስኖና ኢነርጂ ሚኒስትሩ አቶ አለማየሁ ተገኑ በተደጋጋሚ የሚከሰተውን  የሃይል መቆራረጥ በዘላቂነት ለማስወገድ የሚያስችሉ የተለያዩ የመፍትሄ እርምጃዎች እየተወሰዱ መሆኑን ሰሞኑን ለመንግስት መገናኛ ብዙሃን ገልጸዋል፡፡ ሚኒስትሩ አያይዘውም በሃይል ማስተላለፍ ስራ ላይ በተሰማሩ ባለሙያዎች ላይ

መንግስት የጀመረውን ጥብቅ ክትትል አጠናክሮ ይቀጥላል። ሚኒስትሩ አቶ አለማየሁ ተገኑ  እንዳሉት በአገሪቱ ምንም አይነት የሃይል እጥረት ሳይኖር በተደጋጋሚ የሚስተዋለውን የኤሌክትሪክ መቆራረጥ  እልባት ለመስጠት የአጭር ፣የመካከለኛና የረዥም ጊዜ እቅድ  በማውጣት ተግባራዊ እንቅስቃሴ ተጀምሯል

ማለታቸው ይታወሳል። ሚኒስትሩ ይህን ይበሉ እንጂ መብራት ለምን እንደሚቆራረጥ እንኩዋን መ/ቤታቸው ካለማወቁም በተጨማሪ እየተወሰደ ነው የተባለው እርምጃም አስካሁን ምንም ኣይነት የመሻሻል መፍትሔ አለመምጣቱ በተለይ የአዲስአበባን ሕዝብ ተስፋ አስቆርጦአል፡፡

የከተማው ነዋሪ ህዝብ ተስፋ በመቁረጥ በመብራት ኃይል ሰራተኞች ላይ የሃይል ርምጀ አልፎ አልፎ ሲወስድ ይታያል።እንደ ዘጋቢያችን ሪፖርት ብዙዎቹ የመብራት ሃይል ሰራተኞች ለጥገና በሚሄዱበት ወቅት በተበሳጩ ወጣቶች ይደበደባሉ፣ የመብራት ሃይል መኪኖችም እየተሰበሩ ይመለሳሉ።