በአዲስ አበባ በጋራ መኖሪያ ቤቶች ላይ የዋጋ ጭማሪ ተደረገ

ኢሳት ዜና (ሃምሌ 4 ,2009 ) የአዲስ አበባ አስተዳደር በመካከለኛ ገቢ ለሚኖሩ ሰዎች በገነባቸው የኮንደሚኒየም ቤቶች ላይ ያደገው የዋጋ ጭማሪ ተመዝጋቢዎችን ማስቆጣቱ ተነገረ ።

አስተዳደሩ የ972 ቤቶችን እጣ ከማውጣቱ ሁለት ቀናት ቀደም ብሎ መካከለኛ ገቢ ላላቸው የተገነቡ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዋጋን በፊት ከታቀደው 56 በመቶ ጭማሪ አድርጓል ። ለቤቶቹ 11 ሺህ 88 ተመዝጋቢዎች የነበሩ ሲሆን ሁሉም ሙሉ በሙሉ የሚጠበቅባቸውን ክፍያ የፈጸሙ ናቸው ተብሏል ።

የአዲስ አበባ አስተዳደር የቤቶች ልማትና ቁጠባ ድርጅት 972 ቤቶችን ገንብቶ ከነዋሪዎች ተቀማጭ ገንዘቡን ለሚሰበስበው ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አስረክቧል ።

ቤቶቹን ለመገንባት እንደ አውሮፓዊያን አቆጣጠር በ2013 ሲታቀድ ለባለ አንድ መኝታ ቤት 228 ሺህ 900 ብር ፣ ለባለ ሁለት መኝታ ቤት 330 ሺህ ብር ፣ለባለሶስት መኝታ ቤት ደግሞ 386 ሺህ ብር በስኰር ሜትር ለማስከፈል ስምምነት ተደርሶ ነበር ።

ይህም ሆኖ ግን በመሰረተ ልማት ፣ በሰራተኛ ዋጋ መጨመርና በቤቶች የዲዛይን ለውጥ ምክንያት የቤቶቹ ዋጋ ላይ በ56 በመቶ ጭማሪ መደረጉን አስተዳደሩ ይፋ አድርጓል እናም በአዲሱ ዋጋ ተመን መሰረት ለባለ ሁለት መኝታ ቤት 614 ሺህ 602 ብር ፣ ለባለ ሶስት መኝታ ቤቶች 735 ሺህ 241 ብር ፣ ለባለ አራት መኝታ ቤቶች ደግሞ 829 ሺህ 568 ብር እንዲሆን መደረጉን ፎርቹን ጋዜጣ ዘግቧል ።

ይህ ሲሆንም ለባለ 4 መኝታ ቤት ብሎ የተመዘገበ ነዋሪ ባለመኖሩ ለ3 መኝታ ቤት የተመዘገቡ አቅማቸው የሚፈቅድ ከሆነ ወደዚሁ ደረጃ እንደሚሸጋገሩ የአዲስ አበባ የቤቶች ልማትና ቁጠባ ድርጅት አስታውቋል። ይህ ካልሆነ ግን የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተመዝጋቢ የሌላቸውን ባለ አራት መኝታ ቤቶች ለአስተዳደሩ መልሶ እንደሚሸጣቸው ማሳወቁን ዘገባው ጨምሮ ገልጿል ።

ቤቶቹ ሲተላለፉ አቅም የሌላቸው ከተገኙ በተጠባባቂነት የተወስውዱ 20 ባለእጣ እድለኞች በተተኪነት መያዛቸውንም ለማወቅ ተችሏል ። ይህ በእንዲህ እንዳለም የ2013 የቤት ተመዝጋቢዎች ከዚህ ቀደም ከነበረው ዋጋ ተጨማሪ ክፈሉ መባሉ እንዳስቆጣቸውና ከነዋሪዎች ጋር ምክክር ሳይደረግ የዲዛይን ለውጥ ተደርጎ ብትፈልጉ ውሰዱ መባሉ አግባብ እንዳልሆነ መናገራቸውን የኢሳት መንጮች ገልጸዋል ።

የቤቶቹ እጣ ሲወጣ 20 በመቶ ለመንግስት ሰራተኞች 3 በመቶ ለዲያስፖራ ቀሪዎቹ 77 በመቶ ደግሞ ለሁሉም ተመዝጋቢዎች ተደርጎ መከናወኑንም አስተዳደሩ አስታውቋል ።

በ2013 የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ለማግኘት 165 ሺህ ሰዎች ሲመዘገቡ ከነዚሁም መካከል 140 ሺዎቹ በየወሩ እየቆጠቡ እድሉን ለማግኘት በመጠባበቅ ላይ መሆናቸውን ዘገባው አመልክቷል ። ይሁንና በኢትዮጵያ ያለው አገዛዝ የገንዘብ እጥረት ስለገጠመው ቤቶቹን ለመገንባት የበጀት ችግር አለብኝ በሚል ለፓርላማ ባለፈው ሰሞን ማሳወቁ ይታወሳል ።