በእስራኤል ኢትዮጵያውያን ከቀያቸው ተፈናቀሉ

(ኢሳት ዜና –  ሐምሌ 4/2009)  በእስራኤል ማቫሰርት ጺዮን አካባቢ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ናቸው ከቀያችን አላግባብ ተፈናቅለናል ሲሉ በዋና ከተማዋ ቴልአቪቭ በመውጣት ድምጻቸውን ያስሙት

መኖሪያቸውን እንዲለቁ የተሰጣቸው ከሁለት ወራት ያነሰ የጊዜ ገደብም ቢሆን አግባብነት የሌለው ነው ሲሉ ተናግረዋል።

ለተፈናቃዮቹ ጥብቅና የቆመው አካልም የተወሰደው እርምጃ ትክክል አይደለም ሲል ጉዳዩን ለፍርድ ቤት አቅርቧል።

እንደተቆርቋሪው አካል አገላልጽ ከሆነም ለተፈናቃዮቹ መዘጋጃ የሚሆን ተጨማሪ የሶስት አመት የጊዜ ገደብ ሊቀምጥላቸው ይገባል።

ኢትዮጵያውያኑ ከቦታቸው እንዲፈናቀሉ የተደረገውም የእስራኤል የሰራተኞች የጡረታ ፈንድ መስሪያ ቤት ከቤቶቹ ጋር በተያያዘ ያለበትን እዳ ለመክፈል ለግል ተከራዮች ሊሸጥ በመወሰኑ ነው።

እንደመረጃው ከሆነም ቦታው ከባልይዞታው ወደ መስሪያ ቤቱ የተዘዋውረው ከሶስት አመት በፊት ነው ።

ያ የሶስት አመት የጊዜ ገደብ አሁን ላይ የተጠናቀቀ ቢሆንም ለኢትዮጵያውያኑ ተጨማሪ የሶስት አመት የመዘጋጃ ጊዜ ሊቀመጥላቸው ግድ ይላል ብሏል የኢትዮጵያውያኑ ተከራካሪ ናዳቭ ሃይዝኒ።–ለኢትዮጵያውያኑ ቋሚ የመኖሪያ ስፍራ ሊዘጋጅላቸው እንደሚገባ በመጠቆም።

መስሪያ ቤቱ በበኩሉ በእድሜ ገፋ ላሉት ኢትዮጵያውያን አዛውንቶች ተቀያሪ ቦታ ማዘጋጀቱን አስታውቆ ከነሱ ጋር ረጅም አመት በመኖራቸው ቅያሪ ማረፊያ ሊሰጣቸው ይገባል በሚል የቀረበውን ሃሳብ ግን እንደማይቀበለው አስታውቋል።

መስሪያ ቤቱ ይህን ይበል እንጂ ኢትዮጵያውያኑ መፍትሄ ሳይሰጠን ቦታውን አንለቅም፣መብታችን በአግባቡ ሊከበርልን ይገባል ሲሉ በአደባባይ ድምጻቸውን አሰምተዋል።

የሀገሪቱ የስደተኞች ጉዳይ ሚኒስትር መስሪያ ቤት በበኩሉ ቦታው ስደተኞች በትንሹ ለሶስት አመት ያህል ጊዜ እንደማረፊያነት እንዲጠቀሙበት የተዘጀ እንጂ ቋሚ የመኖሪያ ቦታ እንዳልሆን ገልጿል።

ግለሰቦቹን በቦታው ለተጨማሪ ጊዜ በቦታው ማቆየት እንደማይቻል በመጠቆም።

ነገር ግን ኢትዮጵያውያኑ ሜዳ ላይ እንዲወድቁ የሚደረግበት ሁኔታ እንደሌለና ለሚያነሱት ጥያቄም መፍትሄ የሚሆኑ አማራጮችን እንደሚያምቻች ማስታውቁን ኢየሩሳሌም ፖስት ዘግቧል።