በአዲስ አበባና በክልል ከተሞች የቤንዚን እጥረት ተከሰተ

ጥር ፳፰ (ሃያ ስምንት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የቤንዚንና የናፍጣ እጥረቱ በመላ አገሪቱ የተከሰተ ሲሆን በተለይም በአዲስ አበባ፣ በሶማሊ ክልል በጂጂጋ፣ ሀረርና ሌሎችም ከተሞች፣ በደቡብ ደግሞ በሃዋሳ ፣ ሆሳዕና ፣ ወላይታ ሶዶ እና ሚዛን አማን መከሰቱን የደረሰን ዜና ያመለክታል። በጅጅጋ ከሁለት ቀናት በሁዋላ  ነዋሪዎች ነዳጅ ለመቅዳት ሲጋፉ ታይቷል።

ችግሩ የነዳጅ አከፋፋይ ኩባንያዎች ሀላፊነታቸውን በአግባቡ ባለመወጣታቸውና ነዳጁን ማከፋፈል በማቆማቸው የተፈጠረ ነው በማለት የንግድ ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

የኦይል ሊቢያ 48 ያህል ተሽከርካሪዎች ወደ ሌሎች ኩባንያዎች በመሄዳቸው ፤ የነዳጅ አቅርቦት እጥረቱ ከተሽከርካሪ እጥረት ጋር ተያይዞ መምጣቱንም ሚኒስትሩ ገልጸዋል።

ሚኒስትሩ ” የአንዳንድ የነዳጅ ኩባንያዎች ድርጊት በትራንስፖርት እንቅስቃሴው ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ከመፍጠር በዘለለ ክፍለ ኢኮኖሚውን በእጅጉ የሚጎዳ በመሆኑ ፤ ይህን ድርጊት በሚፈፅሙ ኩባንያዎች ላይ አስፈላጊውን እርምጃ ሁሉ መንግስት ለመውሰድ እንደሚገደድ” ገልጸዋል። አከፋፋዮች በበኩላቸው ምንም አይነት ነዳጅ እንዳልቀረበላቸው እየገለጹ ነው።