በአዋሳ ታቦር ትምህርት ቤት የተነሳውን ግጭት ክልሉ ሆን ብሎ ያቀነባበረው እንደነበር አንድ የደኢዴግ አባል ገለጹ

መጋቢት ፳፮ (ሃያ ስድስት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የገዢው ፓርቲ አባል የሆኑት ግለሰብ እንደገለጹት መድረክ የተባለው የተቃዋሚዎች ስብስብ በአዋሳ ከተማ በርካታ ህዝብ በተገኘበት ስብሰባ ማድረጉን ተከትሎ የተበሳጩት የገዢው ፓርቲ ሰዎች ግጭቱን ተቃዋሚዎች ያስነሱት ነው ለማለት ከውጭ የኒፎርም ለብሰው ወደ ትምህርት ቤቱ የገቡ 45 ተማሪዎች 500 ብር ተከፍሎአቸው እንዲነሳ ማድረጉን ገልጸዋል

እቅዱ ሲዘግጀ ነበርኩ ያሉት ግለሰብ፣ ሁኔታው አበሳጭቷቸው ለመናገር እንደተገደዱ ተናግረዋል። ሁሉም የኢህአዴግ አባል ኢህአዴግን ይደግፋል ማለት ኤኢደለም የሚሉት ግለሰቡ፣ ግንባሩ ተቃዋሚዎችን ለመወንጀል የሚሄድበት ርቀት አሳዛኝ ነው ብለዋል።

እቅዱ እንደታሰበው ሳይሳካ መቅረቱን ተከትሎ ደግሞ በነገው እለት የከተማው ነዋሪ ህዝብ ስብሰባ መጠራቱን፣ ህዝቡ ላይወጣ ይችላል በሚል ፍርሃትም እድሮች እንዲቀሰቅሱ መታዘዛቸውን ገልጸዋል።

የነገው ስብሰባ ዋና አላማ ተቃዋሚዎች በምርጫ እንደማያሸንፉ ሲያውቁት የጎዳና ላይ ነውጥና የቀለም አብዮት ለማስነሳት እየጣሩ ነው በሚል ለማውገዝ ነው፡ ሰሞኑን በታቦር ትምህርት ቤት የተነሳውን ግጭት ተከትሎ ታቦርን ጨምሮ፣ ንግስት ፉራ አላሙራና አዳሬ የሚባሉ ትምህርት ቤቶች እንደተዘጉ ነው።

በጉዳዩ ዙሪያ የመስተዳድሩን ባለስልጣናት ለማግኘት ተደጋገሚ ሙከራ ብናደርግም አልተሰካልንም።