በአማራ ብሄር ላይ እየደረሰ ያለው በደል ኢትዮጵያዊነታችንን እየተፈታተነ ነው ሲሉ የአገር ሽማግሊዎች ገለጹ

ሚያዚያ ፲ (አስር) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- መንግስት በክልሉ ነዋሪዎች ላይ የፈጠረው ጥላቻ እና እየወሰደ ያለው እርምጃ የኢትዩጵያዊ ማንነታቸውን እየተፈታተነው እንደመጣ የክልሉ የሀገር ሺማግሌዎች ለመስተዳድሩ ባለስልጣናት አቤቱታ ማቅረባቸው ታውቋል፡፡

የአገር ሽማግሌዎቹ ለአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ባስገቡት ደብዳቤ ላይ እንደተገለጸው በቅርቡ በባህር ዳር ከተማ በህገወጥ መንገድ ተገነቡ የተባሉ ቤቶችን ለማፍረስ በተወሰደ እርምጃ አራት ንፁሃን ዜጎች መገደላቸው አሳፋሪ መሆኑን ጠቅሰዋል።

የንፁሀን ደም ያለአገባብ የፈሰሰ በመሆኑ መንግስት በአስቻኳይ ጉዳዩ ተጣርቶ ሃላፊነቱን እንዲወስድ እና ለተበዳይ ወገኖችም ካሳ እንዲከፍል ሽማግሌዎቹ ጠይቀዋል።

አንድ ሰው ላይ ጥይት ከመተኮስ በፊት ፤ ከማሰርም አስቀድሞ በርካታ አማራጮች እያሉ በሰው ህይዎት ያውም ርዕሰ መሰተዳድሩ ፎቅ ላይ ተቀምጠው እየተመለከቱ በዜጎች ላይ የተፈፀመው ድብደባ፣ የደረሰው የአካል ጉዳትና ግድያ አስነዋሪ መሆኑንም ሽማግሌዎች በደብዳቤያቸው ጠቁመዋል።

ቅሬታ አቅራቢዎች ከክልሉ ርዕሰ መሰተዳድር ጋር ፊት ለፊት ለመነጋገር ያደረጉት ጥረት ሊሰካላቸው አልቻለም። ደብዳቤያቸውን ለክልሉ አስተዳዳሪ በፖሊሶች በኩል ማስረከባቸውን ጉዳዩን በቅርብ ከሚከታተሉት ወገኖች ለማወቅ ተችሎአል። በደብዳቤው ላይ በክልሉ ህዝብ ላይ ተፈጽመዋል የተባሉ በርካታ ችግሮች መዘርዘራቸውን ለደህንነታቸው ሲባል ስማቸውን ያልገለጹ ምንጮች ለኢሳት ተናግረዋል።