በቦና ወረዳ ከ40 በላይ ሰዎች ታፍሰው ተወሰዱ

ግንቦት ፫(ሦስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በሰሜን ጎንደር ዞን በቦና ከተማ ሚያዚያ 29 ቀን ፣ 2005 የተነሳውን ተቃውሞ ተከትሎ ከ40 በላይ ሰዎች በመከላከያ ሰራዊት አባላት ታፍሰው የተወሰዱ ሲሆን ከ8 ያላነሱ ሰዎች ደግሞ በደረሰባቸው ከፍተኛ ደብደባ በጽኑ ቆስለዋል።

ግጭቱ የተፈጠረው በቅጽል ስማቸው አቶ በደሌ የተባሉ ባለሀብት ማህበረሰቡ የሚጠቀምበትን የምንጭ ውሀ በማጠር ለራሳቸው የከብት ማድለብ ስራ ሊጠቀሙበት ማሰባቸውን ህብረተሰቡ በመቃወሙ ነው። ህዝቡ ተቃውሞውን ማሰማት ሲጀምር  ባለሀብቱ  ሰረባ አካባቢ ሰፍሮ የሚገኘውን የመከላከያ ሰራዊት አባላት በማስጠራት በህዝቡ ላይ እርምጃ እንዲወሰድ አስደርገዋል። የመከላከያ አባላቱ በአካባቢው እንደደረሱ ህዝቡን በሰደፍ እና በቆመጥ በመደብደብ በርካቶችን ያቆሰሉ ሲሆን 8 ሰዎች በጽኑ በመቁሰላቸው በአደገኛ ሁኔታ ውስጥ ይገኛሉ።

ወታደሮቹ ከ40 በላይ የሚሆኑ ሰዎችን አፍሰው ወደ አልታወቀ ስፍራ ወስደዋቸዋል። ባሀብትም ባለስልጣንም የሆኑት ግለሰብ የፋሲካ እለት የተወሰኑ የመከላከያ ሰራዊት አባላት በመጥራት በሬ አርደው ማብላታቸውን የአካባቢው ነዋሪዎች ተናግረዋል።

ቤተሰቦቻቸው በከፍተኛ ጭንቀት ውስጥ እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሎአል።

ቦና ከጎንደር ከተማ በ 40 ኪሎሜትር ርቀት ላይ የምትገኘ ከተማ ናት። የቦና ከተማ ባለስልጣናትን ለማግኘት ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም።