በባህርዳር የደረሰውን የቦምብ ፍንዳታ ተከትሎ የብሪታኒያ መንግስት ዜጎቹ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ አሳሰበ

ኢሳት (ታህሳስ 28 ፥ 2009)

በባህርዳር ከተማ በሚገኘው የግራንድ ሆቴል አቅራቢያ የደረሰውን የቦምብ ፍንዳታ ተከትሎ የብሪታኒያ መንግስት ዜጎቹ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ አሳሰበ።

የቦንብ ፍንዳታ መድረሱን ያወሳው የሃገሪቱ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በባህር ዳር ከተማ ሊኖሩ የሚችሉ የብሪታኒያን የአካባቢው ባለስልጣናት የሚሰጧቸውን ምክር እንዲከተሉ ጠይቋል።

የብሪታኒያ መንግስት በባህር ዳር ከተማ የደረሰውን የቦንብ ፍንዳታ አስመልክቶ ለዜጎቹ ማሳሰቢያን ቢያሰራጭም በጥቃቱ የሞተ ሰው እንደሌለ ከመግለጽ ውጪ ዝርዝር መረጃን ከመስጠት ተቆጥቧል።

የሃገሪቱ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአማራ ክልል በተለይም በሰሜን ጎንደር ዞን ያለውን የጸጥታ ችግር ተከትሎ ዜጎች አስፈላጊ ካልሆነ በቀር በክልሉ በሚገኙ ሶስት ዞኖች ጉዞ ከማድረግ እንዲቆጠቡ በተደጋጋሚ ማሳሰቢያ ማውጣቱ ይታወሳል።

ይኸው የጉዞ ማሳሰቢያ የሚቀጥል መሆኑን ያስታወቀው የሃገሪቱ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዜጎቹ ወደ ፀገዴ፣ ምዕራብና ታች አርማጭሆ ከመጓዝ እንዲቆጠቡ በድጋሚ አሳስቧል።

ዕማኞችን ዋቢ በማድረግ ኢሳት ረቡዕ ምሽት በባህርዳር ከተማ በሚገኘው ግራንድ ሆቴል አቅራቢያ የደረሰውን የቦምብ ፍንዳታ መዘገቡ ይታወሳል። ይህንኑ ሁኔታ ተከትሎ የብሪታኒያ መንግስት በጉዳዩ ዙሪያ መግለጫን አውጥቷል፣ ድርጊቱ በከተማዋ አለመረጋጋት መፍጠሩ ተነግሯል።

በኢትዮጵያ ተግባራዊ ተደርጎ የሚገኘውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ምክንያት በማድረግ አሜሪካ ዜጎቿ ወደ ኢትዮጵያ ከመጓዝ እንዲቆጠቡ ማሳሰቢያን ተግባራዊ አድርጋ ትገኛለች።

ይሁንና የኢትዮጵያ ባለስልጣናት ሃገሪቱ እየወሰደችው ያለው ዕርምጃ “ያለውን ዕውነታ ያላገናዘበ” አይደለም ሲሉ ቅሬታን አቅርበዋል። አሜሪካ ተግባራዊ ተደርጎ የሚገኘው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከህዝብ ለተነሱ ጥያቄዎች ምላሽን ከመስጠት ይልቅ የሰብዓዊ መብት ጥሰትን ያባብሳል ስትል ስጋቷን ትገልጻለች።

የአውሮፓ ህብረት እንዲሁም ለስድስት  ወር ያክል ጊዜ ይቆያል የተባለው አዋጅ ስጋት እንዳደረበት ሲገልጽ የቆየ ሲሆን፣ ህብረቱና የተባበሩት መንግስታት የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ከህዝባዊ ተቃውሞ ጋር በተገናኘ ህይወታቸው ያለፉ ሰዎች ድርጊት በገለልተኛ አካል ምርመራ እንዲካሄድበት ጠይቀዋል። ይሁንና፣ መንግስት ጥያቄውን እንደማይቀበለው ገልጿል።