በባህርዳር ከቤት ማፍረስ ጋር በተያያዘ በተነሳ ግጭት ሁለት ሰዎች መገደላቸው ተሰማ

ሚያዚያ ፫ (ሦስት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የከተማው አስተዳደር የቤት አፍራሽ ግብረሃይል በቀበሌ 13 በህገወጥ መንገድ ተሰርተዋል ያላቸውን ቤቶች ለማፍረስ በተንቀሳቀሰበት  ወቅት ከነዋሪዎች ጋር በተፈጠረ ግጭት 2 ሰዎች በፌደራል ፖሊሶች ሲገደሉ ሌሎች ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ደግሞ ጉዳት ደርሶባቸዋል።

የአካባቢው ነዋሪዎች እንደገለጹት ቤት አፍራሽ ግብረሃይሎች ነዋሪዎች ዛሬውኑ ቤታቸውን እንዲያፈርሱ ሲጠይቋቸው፣ ነዋሪዎች  ” መጪው የአመት በአል ጊዜ ነው፣  ክረምትም እየመጣ ነው፣ ቤታችን አፍርሰን የት እንወድቃለን” በማለት ሲመልሱ፣ አፍሪአሽ ግብረሃይሉ የነዋሪዎች አቤቱታ ባለመቀበል ወደ ሃይል እርምጃ ተንቀሳቅሷል። ህዝቡ በድንጋይ ራሱን ለመከላከል ሙከራ ሲያደርግ ፖሊሶች ” ጦርነት ውስጥ የገቡ ይመስል በተደጋጋሚ ጥይቶችን በመተኮስ በነዋሪዎች ላይ ጉዳት አድርሰዋል” ሲሉ ስማቸው እንዳይጠቀስባቸው የፈለጉ ነዋሪዎች ተናግረዋል። ኢሳት አንድ ሰው መሞቱን ሲያረጋገጥ ስለአንደኛው ግለሰብ ተጨማሪ ማስረጃ እያሰባሰበ ነው። የክልሉ ፖሊስ ህዝብ ግንኙነት ሃላፊ ኮማንደር ሰይፉን ለማነጋገር ብንሞክርም ስብሰባ ላይ በሚል መልስ ሊሰጡን አልቻሉም።