በቁጫ ወረዳ ከተነሳው ተቃውሞ ጋር በተያያዘ በርካታ ትምህርት ቤቶች ተዘጉ

ጥቅምት ፳፰(ሃያ ስምንት )ቀን ፳፻፮ / ኢሳት ዜና :-በደቡብ ክልል በቁጫ ወረዳ የሚማሩ ተማሪዎች ከማንነት እና መብት መከበር ጋር በተያያዘ ያነሱትን ተቃውሞ ተከትሎ በርካታ የአንደኛ እና መለስተኛ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች ትምህርት ማቆማቸውን የአካባቢው ነዋሪዎች ተናግረዋል።

ተማሪዎቹ በቋንቋችን እንማር፣ በአካባቢያችን የሚታየው የመብት ረገጣ ይቁም የሚሉ ጥያቄዎችን ማንሳታቸውን የሚናገሩት ነዋሪዎች፣ የፌደራል ፖሊስ አካባቢውን ከተቆጣጠረው በሁዋላ ቁጥራቸው ከ25 እስከ 40 የሚደርሱ ተማሪዎችን ይዞ አስሯል።

ውጥረቱ አሁንም የቀጠለ ሲሆን ፣ ቀደም ብሎ ያለበቂ ምክንያት ታስረው የተፈቱት 40 ሰዎች በዛሬው እለት ተመልሰው እንዲታሰሩ ተደርጓል።

መምህራን ትናንትና ዛሬ ስብሰባ ላይ የነበሩ ሲሆን፣ የአካባቢው ባለስልጣናት ለተፈጠረው ችግር መምህራንን ተጠያቄ አድርገዋል። ባለስልጣናቱ ” ለኢሳት፣ ለጀርመን ወይም ለአሜሪካ ሬዲዮ ከመናገር ውጭ ምንም የምታመጡት ነገር የለም መባላቸውን ያነጋጋርናቸው አንድ መምህር ገልጸዋል ።  የአካባቢውን የፖሊስ ሀላፊዎች ለማግኘት ያደረግነው ጥረት አልተሳካም።