በሰርባ መስኖ ተፋሰስ ፕሮጀክት ላይ ጥቃት ፈጽመዋል በተባሉ የአርበኞች ግንቦት ሰባት ታጣቂዎች ላይ ክስ ተመሰረተ

(ኢሳት ዜና–መስከረም 10/2010) የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ በሰርባ መስኖ ተፋሰስ ፕሮጀክት ላይ ጥቃት ፈጽመዋል ባላቸው የአርበኞች ግንቦት ሰባት ታጣቂዎች ላይ ክስ መሰረተ።

 

በክስ መዝገቡ ላይ እንደተብራራው ታጣቂዎቹ በፈጸሙት ጥቃት ሁለት ሰዎች ሲገደሉ አምስት ቆስለዋል።

ባለፈው ዓመት መጋቢት 25/2009 ተፈጸመ የተባለውን ጥቃት በወቅቱ የአርበኞች ግንቦት ሰባት ንቅናቄ ሃላፊነት እንደሚወስድ መግለጹን መዘገባችን ይታወሳል።

 

መጋቢት 25 2009 የአርበኞች ግንቦት ሰባት ታጣቂዎች በሰሜን ጎንደር ዞን በደምቢያ ወረዳ ሰርባ በሚገኘው የመስኖ ፕሮጀክት ላይ ጥቃት በፈጸሙበት ወቅት፡ ፕሮጀክቱ የህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ ህወሀት ንብረት የሆነው የትግራይ መልሶ ማቋቋሚያ ድርጅት ኢፈርት የሚያከናውነውና ከፍተኛ የህዝብ ሀብት በዘረፋ ለህወሀት የሚገባበት መሆኑ በምክንያትነት ተጠቅሷል።

በህዝብ ማዕቀብ የተደረገበት የዳሽን ቢራ ለማጥመቂያ የሚሆነውን ግብዐት የሚያበቅልበት የመስኖ ፕሮጀክት መሆኑም ለጥቃት ኢላማ መደረጉን በወቅቱ መዘገቡ ይታወሳል።

በዚህም ከስርዓቱ ጋር የጥቅምና የዓላማ ግንኙነት አላቸው በተባሉ የፕሮጀክቱ አመራሮች ላይ እርምጃ መውሰዱን አርበኞች ግንቦት ሰባት አስታውቋል።

የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ ይህን ጥቃት ፈጽመዋል ባላቸው 14 ግለሰቦች ላይ ክስ መመስረቱን ሪፖርተር ጋዜጣ ዘግቧል።

የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ የክስ መዝገብ ላይ እንደተገለጸው ተከሳሾቹ የአርበኞች ግንቦት ሰባት ድርጅት አባልና ታጣቂ በመሆን፣ በሰሜን ጎንደር ዞን ደምቢያ ወረዳ መንድባ ጫካ ውስጥ ወታደራዊ ቤዝ በመመሥረትና ሙሉ የጦር መሣሪያ በመታጠቅ፣ ከኤርትራ በመጡ አመራሮች ፖለቲካዊና ወታደራዊ ስልጠና ወስደዋል።

ተከሳሾች በመጋቢት ወር 2009 በመንድባ ጫካ ውስጥ ከተሰበሰቡ በኋላ ባደረጉት ምክክር፣ መንግሥት በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር ዞን ደምቢያ ወረዳ ውስጥ በቻይና ኮንትራክተሮች እያስገነባ ባለው የሰርባ የመስኖ ተፋሰስ ፕሮጀክት ላይ የሽብር ጥቃት ለመፈጸም መስማማታቸውን የዓቃቤ ሕግ ክስ ያብራራል፡፡

መጋቢት 25 2009 ከሌሊቱ ሰባት ሰዓት አካባቢ እነዚህ ተከሳሾች ጥቃት በመፈጸም ሁለት ሰው መግደላቸውንና አምስቱ ላይ ከባድ የአካል ጉዳት መድረሱንም የአቃቤ ክስ ላይ ተጠቅሷል።

ጠቅላላ ግምቱ 1,933,760 ብር በሚገመት ንብረት ላይ ውድመት መድረሱም ተጠቁሟል።

በአዲስ አበባ ፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት መታየት በጀመረው በዚሁ ክስ 14ቱ ግለሰቦች በሌላም ተቋም ላይ ጥቃት በመፈጸም ተወንጅለዋል።

ሚያዝያ 12 2009 በሰሜን ጎንደር ዞን ደምቢያ ወረዳ ጉራምባ ቀበሌ በሚገኝ የአማራ ውኃ ሥራዎች ኮንስትራክሽን ድርጅትና ማሽኖች ላይ ጥቃት በመፈጸም ግምቱ 134,686 ብር የሆነ ንብረት ላይ ጉዳት ማድረሳቸውን የዓቃቤ ሕግ ክስ ያትታል።

ተከሳሾቹ አባላት በመመልመል በአካባቢው በሚገኝ ጫካ ውስጥ የማደራጀት፣ የማስታጠቅና ወታደራዊ ሥልጠና እንዲወስዱ በማድረግ በሚልም ተከሰዋል።

ሌሎች ተፈጽመዋል የተባሉ ድርጊቶችን በመጥቀስ አቃቤ ህግ በ14ቱ ግለሰቦች ላይ የሽብረትኝነት ክስ ማቅረቡን ነው ከሪፖርቱ ለማወቅ የተቻለው። ቀጣዩ የፍርድ ቤት ቀጠሮ ለጥቅምት 2 2010 ሆኖ የዕለቱ ችሎት አብቅቷል።

የህወሀት መንግስት ጥቃቱን የፈጸሙት እነዚህ ግለሰቦች ናቸው በሚል ክስ ቢመሰርትባቸውም ስርዓቱ የሚያመልጠኝ የለም ለሚል የፕሮፖጋንዳ ፍጆታ በጥቃቱ ያልተሳተፉትን በመያዝ ክስ የሚመስርትበት የተለመደ ተግባር መሆኑን ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ወገኖች ይገልጻሉ።