በመጪው እሁድ በሚካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ ላይ የቅስቀሳ ወረቀቶችን በመበተን ላይ የነበሩ የአንድነት ፓርቲ አባላት ታሰሩ

መጋቢት ፳፭ (ሃያ አምስት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የአዲስ አበባ መስተዳደር የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ሃለፊ ሆኑት አቶ ያሬድ አማረ ለኢሳት እንደገለጹት ምንም እንኳ የተወሰኑ ሰዎች የታሰሩ ቢሆንም፣ ቅስቀሳው በጥሩ ሁኔታ እየተካሄደ መሆኑን ገልጸዋል።

አቶ ሀብታሙ ታምሩ፣ አሸናፊ ጨመረዳ እና ደራሲ መቶ አለቃ አንዳርጌ መስፍን የቅስቀሳ ወረቀቶችን ሲበትኑ ተይዘው የካ ፖሊስ ጣቢያ ታስረዋል።

ለገሃር ፖሊስ ጣቢያ አካባቢ ደግሞ አክሊሉ ሰይፉና ሰለሞን ጸሃየ መጠነኛ ድብደባ እንደተፈጸመባቸውም አቶ ያሬድ አማረ ገልጸዋል ። ታሪኬ ኬባና ኤፍሬም ሰለሞን በተባሉትም ላይ ሲቪል ለባሽ የደህንነት ሰራተኞች ሊመቱዋቸው ሲሞክሩ ህዝቡ መብታቸው ነው በሚል ተከላክሎላቸዋል።

የአዲስ አበባ መስተዳደር የሰላማዊ ሰልፍ ክፍል አንድነት ፓርቲ ላቀረባቸው የተለያዩ አማራጭ የመሰለፊያ ቦታዎች ፈቃድ የከልከለ መሆኑን ቢገልጽም አቶ ያሬድ ግን ሰላማዊ ሰልፉ መጀመሪያ በተያያዘለት ቦታ ላይ ይካሄዳል ብለዋል

አንድነት ፓርቲ መጋቢት 28 ፣ 2006 ዓም ቀበና ከሚገኘው የፓርቲው ጽህፈት ቤት ተነስቶ መጨረሻውን ጠ/ሚንስትሩ ጽህፈት ቤት የሚያደርግ ሰላማዊ ሰልፍ መጥራቱ ይታወቃል።

የከተማው ህዝብ በነቂስ ወደ አደባባይ ወጥቶ ውሃ፣ መብራትና ትራንስፖርት ችግሮች እንዲቀረፉለት እንዲጠይቅ አንድነት ጥሪ ማቅረቡ ይታወቃል።

አንድነት ፓርቲ ከወር በፊት በባህርዳር ከተማ እጅግ በርካታ ህዝብ በተገኘበት የተቃውሞ ሰልፍ ማድረጉ ይታወቃል። በእሁዱም ሰልፍ እንዲሁ ህዝቡ በብዛት ተገኝቶ ድምጹን እንደሚያሰማ የፓርቲው አመራሮች ተስፋቸውን እየገለጹ ነው።