በመርዓዊ ከተማ በመቶዎች የሚቆጠሩ ህጻናትና አርሶደአሮች ታሰሩ

መጋቢት ፲፯ (አስራ ሰባት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በምእራብ ጎጃም ዞን በሜጫ ወረዳ በእናሸንፋለን ቀበሌ በጨቦች ጎጥ  ለአበባ ምርት በሚል የከርሰ ምድር ውሃ ለማውጣት መንግስት እንቅስቃሴ መጀመሩን የተቃወሙ ቁጥራቸው ከ200 እስከ 300 የሚደርስ አርሶ አደሮች፣ እድማያቸው ከ9 እስካ 12 የሚደርስ ታዳጊዎች፣ ሴቶችና ወጣቶች በገፍ ተይዘው በመርዓዊ ከተማ እና በዱርቤቴ እስር ቤቶች መታሰራቸውን ለማወቅ ተችሎአል።

ባለፈው ሃሙስ ፕሮጀክቱን የተቃወሙ አርሶደሮች በጉድጓድ መቆፈሪያ ማሽኑ ላይ ጉዳት ማድረሳቸውን ተከትሎ ከባህርዳር የመጡት የፌደራል ፖሊሶች በአርሶ አደሮች ላይ ጭካኔ የተሞላበት እርምጃ ወስደዋል። አካባቢው አሁንም በፖሊስ የተከበበ ሲሆን በርካታ ወጣቶችም ተሰደዋል።

ጉዳዩን  በማስመልከት ጥያቄ ያቀረብንላቸው የወረዳው የመኢአድ ሰብሳቢ አቶ ስማቸው ምንችል ፣ የአካባቢው ህዝብ ቀደም ብሎ ተቃውሞውን ያቀረበ ቢሆንም፣ መንግስት ግን የህዝብን ተቃውሞ ወደ ጎን በማለት ፕሮጀክቱን ተግባራዊ ለማድረግ መንቀሳቀሱን ገልጸዋል።

እስር ቤቶችን ሄደው መጎብኘታቸውን የሚገልጹት አቶ ስማቸው የእስረኞች አያያዝ እጅግ አሳዛኝ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህ ወረዳ ከዚህ ቀደም ከአበባ እርሻ ጋር በተያያዘ በርካታ አርሶደሮች ታስረው እንደነበር ኢሳት መዘገቡ ይታወሳል።

በጉዳዩ ዙሪያ የወረዳውን ባለስልጣናት ለማነገጋገር ያደርግነው ሙከራ አልተሳካም።