በሌብነት የተጠረጠሩ አራት የኮንስትራክሽን ድርጅት ባለቤቶች ከሀገር ማምለጣቸው ታወቀ

(ኢሳት ዜና–መስከረም 16/2010) በሌብነት የተጠረጠሩ አራት የኮንስትራክሽን ድርጅት ባለቤቶች ከሀገር ማምለጣቸው ታወቀ።

ሆኖም በሌሉበት በአራቱም ላይ ባለፈው ሳምንት ክስ መመስረቱ ታውቋል።
የኮንስትራክሽን ድርጅቶቹ ከኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን ሃላፊዎች ጋር በመሆን በ2 ቢሊየን 150 ሚሊየን ብር ዘረፋ ተጠያቂ መሆናቸው ተመልክቷል።

በሌብነት ተጠርጥረው ሲፈለጉ ከሀገር በማምለጣቸው ፍርድ ቤት ያልቀረቡት የሳትኮን ኮንስትራክሽን ባለቤት አቶ ሳሙኤል ተክላይ፣የገምሹ ኮንስትራክሽን ባለቤት አቶ ገምሹ በየነ እንዲሁም የዲ ኤም ሲ ኮንስትራክሽን ባለቤት አቶ ዳንኤል ማሞና የሀዚ አይ አይ ኮንስትራክሽን ድርጅት ባለቤት አቶ ዛካር አህመድ መሆናቸው ታውቋል።

መስከረም 12/2010 ከኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ከነበሩት ከአቶ ዛይድ ወልደገብርኤልና ከሌሎች የባለስልጣኑ መስሪያ ቤት ሰራተኞች ጋር ክስ የተመሰረተባቸው አራቱ የድርጅት ባለቤቶች 2 ቢሊየን 150 ሚሊየን 382 ሺ 208 ብር የሀገር ሃብት በመዝረፍ በጋር ተጠያቂ መሆናቸው ተመልክቷል።

የኮንስትራክሽን ድርጅት ባለቤቶቹ ድንገት ለስራም ይሁን ለእረፍት በወጡበት ቀሩ ወይንስ መረጃው ሲደርሳቸው አስቀድመው ወጡ የሚለው ምላሽ አላገኘም።

አንዳንድ የውስጥ ምንጮች እንደሚገልጹት ተጠቃሽ የኩባንያ ባለቤቶቹ እንዲወጡ የተደረጉት ሆን ተብሎ እንደሆነም ጥርጣሬ አለ።

የግለሰቦቹ መያዝ የሕወሃት ቡድን ሊያስራቸው የማይፈልጋቸውን ባለስልጣናት ስለሚያነካካ ሰዎቹ አስቀድመው እንዲወጡ ተደርገዋል።

የኢሊሊ ሆቴል ባለቤትና የገምሹ በየነ ኮንስትራክሽን ባለቤት የአቶ ገምሹ በየነ መያዝ ከቀድሞው ገንዘብ ሚኒስትር አቶ ሶፊያን አህመድና ከአፈጉባኤ አባዱላ ገመዳ ጋር የተያያዘ በመሆኑ ለግዜው ሰዎቹ ስለሚያስፈልጉ አቶ ገምሹን እንዲወጡ ማድረግ አማራጭ ተደርጎ ተወስዷል።

የዲ ኤም ሲ ባለቤት አቶ ዳንኤል ማሞም ከጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ጋር የጥቅም ግንኙነት ስላላቸው በተመሳሳይ እንዲወጡ ተደርጓል።

የሳትኮን ባለቤት አቶ ሳሙኤል ተክላይ በሕወሃት ቡድን ውስጥ በአንጃነት ከቆመውና እየተገፋ ካለው ከአቶ ስብሃት ቡድን ጋር በመሆናቸው በድንገት በወጡበት መቅረታቸው ተመልክቷል።