በሊቢያ አፍሪካውያን ስደተኞች እንደሚሸጡ፣እንደሚለወጡና እንደሚገደሉ ታወቀ

(ኢሳት ዜና–ሕዳር 20/2010)በሊቢያ በአንድ ሳምንት ብቻ በመቶዎች የሚቆጠሩ አፍሪካውያን ስደተኞች እንደሚሸጡ፣እንደሚለወጡና እንደሚገደሉ ታወቀ።

በመንግስታቱ ድርጅት የፈረንሳይ አምባሳደር እንዲህ አይነቱን ህገወጥ ድርጊት ድርጅቱ ማስቆም አለበት በህገወጥ ድርጊቱ ተሳታፊዎች ላይም ማዕቀብ መጣል አለበት ብለዋል።

ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከተው ጥርስ አልባው የአፍሪካ ህብረት ግን በአቢጃን ኮትድቯር ከአውሮፓ ህብረት ጋር የጋራ ጉባኤ በማካሄድ ላይ ነው።

በሊቢያ እየተካሄደ ያለው የባሪያ ንግድ ከሁለት ሳምንት በፊት በሲ ኤን ኤን ይፋ ከሆነ በኋላ በሌሎች መገናኛ ብዙሃንና በአለም አቀፍ ማህበረሰብ ዘንድ መነጋገሪያ ሆኗል።

በተባበሩት መንግስታት የፈረንሳይ አምባሳደር ድርጅቱ በሕገወጥ ድርጊቱ ተሳታፊ በሆኑት ላይ ማዕቀብ እንዲጥል ዛሬ ጠይቀዋል።

በዚሁ በባሪያ ንግድ ላይ አስቸኳይ ስብሰባ የተቀመጠው የመንግስታቱ ድርጅት አለም አቀፍ ህግጋትንና ሌሎች መንገዶችን ተጠቅሞ ሕገወጥ አዘዋዋሪዎችንና የባሪያ ንግድ ፈጻሚዎችን በአለም አቀፍ ወንጀለኞች ፍርድ ቤት ለማቆም የሚቻልበትን መንገድ ለመወያየት ነበር።

ስብሰባው ግን አቋም ሳይወስድ ተበትኗል።

የባሪያ ፍንገላና ሕገወጥ የሰዎች ዝውውር በሊቢያ ለረጅም ጊዜ የነበረ ችግር ነው ይላል ኦማር ቱርቢ ለአልጀዚራ ሲናገሩ።

ጋዳፊ በስልጣን ላይ በነበሩበት ወቅት እንኳን የሕገወጥ መሳሪያና ዕጽ ዝውውር፣የሰዎች ዝውውርና ተዛማጅ ወንጀሎች አስቸጋሪ ጉዳዮች እንደነበሩ ይናገራሉ ከአሜሪካ መንግስት ጋር በመተባበር በሕይወት አድን ስራ ላይ ተሳትፈው የነበሩት ኦማር ቱርቢ።

በ2011 በአሜሪካ መራሹ ሃይል ሙአመር ጋዳፊ ከስልጣን ከተወገዱ በኋላ ሊቢያ በእርስ በርስ ጦርነት ስትታመስ ለሕገወጥ አዘዋዋሪዎችና የባሪያ ፈንጋዮች አመቺ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው ይነገራል።

በተባበሩት መንግስታት እውቅና የተሰጠው የብሔራዊ ሽግግር ምክር ቤት በዛ ያሉ ግዛቶችን ሲቆጣጠር የአይሲስና አልቃይዳ ቡድኖችም እንዲሁ ሰፋ ያሉ ግዛቶችን ተቆጣጥረው ይገኛሉ።

ከሁለት ሳምንት በፊት በሲ ኤን ኤን የወጣው የምስል ዘገባ በሊቢያ ከምዕራብ አፍሪካ የመጡ ስደተኞች በጨረታ በአማካኝ በ400 ዶላር ሲሸጡ ያሳያል። “ጠንከር ያሉ ልጆች ለእርሻ ስራ” ይላል አጫራቹ ተጫራቾችም የሚገዙበትን ዋጋ በውርርድ እየጨመሩ ይናገራሉ።

ባሪያ ፈንጋዮቹ ስደተኞቹን ባዳዬ ብለው ይጠሯቸዋል።ሸቀጥ እንደማለት ነው በአረብኛ ።

በሊቢያ በአንድ ሳምንት ብቻ በመቶዎች የሚቆጠሩ አፍሪካውያን ስደተኞች እንደሚሸጡ፣እንደሚለወጡና እንደሚገደሉ ነው መረጃዎች የሚያመለክቱት።

በሊቢያ የስደተኞች ማጎሪያ ውስጥ ያሉትን አፍሪካውያን የሚያሳዩ በሲ ኤን ኤንም ሆነ በሌሎች መገናኛ ብዙሃን የቀረቡ ምስሎች ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን እንደሚገኙበት ለማወቅ ተችሏል።

በአቢጃን ኮትዲቯር እየተካሄደ ያለው የአውሮፓ ህብረትና ጥርስ አባው የአፍሪካ ህብረት የጋራ ጉባኤ በሊቢያ ያለውን የባሪያ ፍንገላ በገለልተኛ ወገን እንዲጣራ የሚጠይቅ ሰነድ ያወጣል ተብሎ ይጠበቃል።

በአውሮፓ ከተሞች ባሉ የሊቢያ ኤምባሲዎችም የተቃውሞ ሰልፎች በመደረግ ላይ ናቸው።

ለባሪያ ንግድና ሕገወጥ ዝውውር ዜጎቻቸው የተዳረጉባቸው የአፍሪካ መንግስታት ስደተኞቹን ከሊቢያ ለማውጣት እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ ናቸው።

በአለም አቀፍ መገናኝ ብዙሃን ከሊቢያ በሚወጡ ምስሎች ኢትዮጵያውያን በግልጽ እንዳሉበት ቢታይም ለህዝቡ ግድ የሌለው የወያኔ አገዛዝ ዜጎቹን ስለመታደግ እስካሁን ያለው ነገር የለም።