በለንደን የሚገኙ ኢትዮጵያውያን የተቃውሞ ሰልፍ አድረጉ

ሐምሌ ፲፩(አስራ አንድ)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ኢትዮጵያውያኑ በእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ፊት ለፊት በመገኘት ፣ የኢህአዴግ መንግስት በግንቦት7 ዋና ጸሃፊ በአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ላይ

በወሰደው ህገወጥ እርምጃ የእንግሊዝ መንግስት ጠንካራ እርምጃ እንዲወስድ ጠይቀዋል። በስፍራው የነበረውን ዘጋቢያችን ወንድማገኝ ጋሹን አነጋግረነዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ፎሬን ፖሊሲ መጽሄት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን በተመለከተ ሰፊ ዘገባ አቅርቧል። በምስራቅ አፍሪካ የሚገኙ አሸባሪዎችን እንዲዋጋላቸው በሚል ኢህአዴግን የሚደግፉት

አሜሪካና እንግሊዝ፣ አገዛዙ በዜጎቹ ላይ በሚፈጽመው ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት አጣብቂኝ ውስጥ መግባታቸውን ገልጿል።

አቶ አንዳርጋቸው በኢትዮጵያ ውስጥ ዲሞክራሲያዊ ስርአት እንዲገነባ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረጉን የገለጸው መጽሄቱ፣ ገዢው ፓርቲ  በሽብርተኝነት ስም ፖለቲከኞችን በመክሰስና አፍኖ በመውሰድ

ለዲሞክራሲ የሚደረገውን ትግል ለማፈን ሙከራ ያደርጋል ብሎአል።

የአቶ አንዳርጋቸውን መያዝ ተከትሎ ኢትዮጵያውያን አሁንም ቁጫቸውን እየገለጹ ነው።

በህዝቡ እንቅስቃሴ የተደናገጠው ገዢው ፓርቲ፣ አቶ አንዳርጋቸው ያሉበትን ሁኔታ ይፋ ለማድረግ ወይም በዘመዶቻቸውና በዲፐሎማቶች እንዲጎበኙ ለማድረግ አልደፈረም።

ከአስር ቀናት በፊት የወንድማቸውን ጉዳይ ለመከታተል ከአሜሪካ ወደ ኢትዮጵያ ያቀኑት የአቶ አንዳርጋቸው ታላቅ እህት ወ/ሮ ብዙአየሁ ጽጌ በ24 ሰአታት ውስጥ አገር ለቀው እንዲወጡ መደረጋቸው ይታወቃል።