በሀረር ከተማ በእስር ላይ የሚገኙ ዜጎች ከፍተኛ ድበደባ እየተካሄደባቸው ነው

መጋቢት ፳፪ (ሃያ ሁለት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የእስር ቤት ምንጮች እንደገለጹት በሀረር ከደረሰው ተደጋጋሚ ቃጠሎ ጋር በተያያዘ ተቃውሞቸውን አሰምተዋል በሚል የታሰሩት በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በፌደራል ደህንነት መርማሪዎች ከፍተኛ ድብደባ እየተካሄደባቸው ነው:፡

ፖሊስ ጋራጅ ውስጥ የታሰሩት ወጣቶች ከምግብ ተከልክለው ከዘመድ እንዳይገናኙ ተደርገው ” እመኑ” በሚል ከፍተኛ ድብደባ እየተፈጸመባቸው ነው። ታከሉ ሙላቱ፣ ታገሰ ሙላቱና አዳነ የሚባሉ የጫማ ንግድ ድርጅት ባለቤቶች ከፍተኛ ድበደባ ተፈጽሞባቸው ራሳቸውን ስተው እንደነበር የእስር ቤት ምንጮች ገልጸዋል። በተለይ ታከለ ሙላቱ የተባለው ነጋዴ  ወደ ጀጉላ ሆስፒታል ቢወሰድም፣ ከሆስፒታል በሁዋላ የት እንደተወሰደ አልታወቅም።

በጥይት ተደብድበው የሞቱ ሰዎች መኖራቸውንም ምንጮች አክለው ገልጸዋል። ተወከል የሚባል ወጣት ደረቱ አካባቢ በጥይት ተመትቶ በህክምና ላይ ነው።

ገንዘብ አላቸው የሚባሉ ነጋዴዎችን ደግሞ ” ተጠርጣሪዎች ናችሁ” በሚል እየታሰሩ ፣ ፖሊሶች ጉቦ እየተቀበሉ እየለቀቁዋቸው መሆኑን ምንጮች አክለው ገልጸዋል።

መስተዳድሩ በቅርቡ በሃረር የደረሰውን  የእሳት አደጋ መነሻ በተመለከተ የተለያዩና የተምታቱ መግለጫዎችን እየሰጠ ነው።