ሲአን አባሎቹ በመገደላቸውና በመታሰራቸው ከእሁዱ ምርጫ ራሱን ማግለሉን አስታወቀ

ሚያዚያ ፬  (አራት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:- የድርጅቱ ዋና ጸሀፊ ለኢሳት እንደገለጡት ከ787 በላይ አባሎቻቸው በመታሰራቸውንና ባለፈው ሳምንት በዳሌ ወረዳ እጩ ተወዳዳሪው ተሾመ ካሰና የሚባል ሰው ተገድሎ በመገኘቱ እንዲሁም የሲአን አባላትን ማዋከብ፣ ከስራ ማፈናቀል እና ተማሪዎችን ማባረሩ በመቀጠሉ ድርጅቱ ራሱን ለማግለል መወሰኑን ዋና ጸሀፊው አቶ ለገሰ ላንቃሞ ተናግረዋል።

የፌደራል ፖሊስ አባላት በአካባቢው ተሰማርተው በድርጅቱ አባሎች ላይ ወከባ እየፈጸሙ መሆኑን ዋና ጸሀፊው ተናግረዋል። መንግስት ከምርጫው እንዳይወጡ ለምኖአቸው እንደነበርም ዋና ጸሀፊው ገልጸዋል።

ሲአን የሲዳሞ አካባቢ የክልል አስተዳደር መብት እንዲሰጠው በተደጋጋሚ ሲጠይቅ መቆየቱ ይታወሳል።