ሱዳን ተጨማሪ ወታደሮቿን ወደ ኤርትራ ድንበር አስጠጋች

(ኢሳት ዲሲ–ጥር 7/2010)

ከግብጽ ጋር ውዝግብ ውስጥ የገባችው ሱዳን ተጨማሪ ወታደሮቿን ወደ ኤርትራ ድንበር ከሰላ ማስጠጋቷን የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገለጸ።

ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ወርቅነህ ገበየሁ ጋር ትላንት በሱዳን ካርቱም የተገናኙት የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢብራሂም ጋንዱር ርምጃውን የወሰድነው በደረሰን መረጃ ላይ ተመስርተን ነው ብለዋል።

በወሩ መጀመሪያ ላይ ከኤርትራ ጋር የሚያዋስናትን ድንበር ሙሉ በሙሉ የዘጋችው ሱዳን ቀደም ሲል በሺዎች የሚቆጠሩ ወታደሮችን ወደ ኤርትራ ድንበር ማስጠጋቷ ይታወሳል።

ሱዳን ወታደሮቿን ወደ ኤርትራ ድንበር ያስጠጋችው የግብጽ ወታደሮች ኤርትራ መግባታቸውን ተከትሎ እንደሆነም ይታወሳል።

ግብጽ ወታደሮቿን ወደ ኤርትራ የላከችበትና ከሱዳን ጋር ውዝግቡ የተካረረበት ሁኔታ የተከተለው ሱዳን ከቱርክ ጋር ባደረገችው ስምምነት ምክንያት እንደነበርም አልጀዚራ በዘገባው አስታውሷል።

የቱርኩ ፕሬዝዳንት ሬሲፕ ጣይብ ኤርዶጋን በታህሳስ በካርቱም ከሱዳን ፕሬዝዳት ጄኔራል ኦማር አልበሽር ጋር ያደረጉት ስምምነት ግብጽን አስቆጥቷል።

ሱዳን ሱአኪን የተባለውን ደሴቷን ለቱርክ አሳልፋ መስጠቷና ይህም ቱርክ በቦታው ወታደራዊ ሰፈር ልትገነባ ነው የሚል ጥርጣሬ መከተሉ ካይሮና ካርቱምን ከፍተኛ ውዝግብ ውስጥ አስገብቷል።

በሕጋዊ መንገድ በግብጽ ሕዝብ ምርጫ ወደ ስልጣን የወጡት ፕሬዝዳንት መሀመድ ሙርሲ በጄኔራል አልሲሲ መፈንቅለ መንግስት መባረራቸውን ቱርክ ተቃውማለች።

በዚህም በግብጽና በቱርክ መካከል ጤናማ ግንኙነት አለመኖሩ አሁን ለተፈጠረው ቀውስ በምክንያትነት ከሚጠቀሱት ጉዳዮች አንዱ ሆኗል።

ቱርክ በሱዳን የጦር ሰፈር ማግኘቷን ተከትሎ ግብጽ በመቶዎች የሚቆጠሩ ወታደሮቿን ወደ ኤርትራ በመላክ በሱዳን ድንበር በኩል አስፍራለች።

ሱዳንም በሺዎች የሚቆጠሩ ወታደሮቿን ወደ ኤርትራ ድንበር ከማስጠጋቷም ባሻገር ከኤርትራ ጋር የሚያዋስናትን ድንበር ሙሉ በሙሉ ዘግታለች።

የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢብራሂም ጋንዱር ተጨማሪ የሱዳን ወታደሮች ከኤርትራ ጋር በሚዋሰኑበት ከሰላ ማስጠጋታቸውን ትላንት ይፋ አድርገዋል።

ርምጃውም የተደቀነውን ስጋት ለመከላከል እንደሆነም ጠቁመዋል።

የሱዳንና የግብጽ ውዝግብ ኢትዮጵያና ኤርትራንም በተዘዋዋሪ እያሳተፈ ይገኛል።

የኤርትራው ፕሬዝዳት ኢሳያስ አፈወርቂ ባለፈው ሳምንት ወደ ካይሮ ሲሄዱ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ወርቅነህ ገበየሁ ትላንት ካርቱም ገብተዋል።

የሱዳን ጦር ሃይሎች ኢታማዦር ሹም ባለፈው ሳምንት አዲስአበባ መሄዳቸው ሲታወስ ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ደግሞ ዛሬ ካይሮ ይገባሉ ተብሎ ቢጠበቅም ባልታወቀ ምክንያት ጉዞው ወደ ረቡዕ መሻገሩ ተሰምቷል።

የግብጽ ወታደሮች ኤርትራ ገብተዋል በሚል አልጀዚራ የዘገበው የኤርትራው ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ የፈጠራ ዜና ነው ሲሉ አጣጥለውታል።