ሰሞኑን የሐመር አርብቶ አደሮች ራሳቸውን ከፖሊስ ጥቃት ለመከላከል በወሰዱት የመልሶ ማጥቃት እርምጃ፤ ከደርዘን በላይ የሚሆኑ የፖሊስ ሀይሎችን ሙትና  ቁስለኛ ማረጋቸው ተመለከተ።

ጥር ፲፬(አስራ አራት ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ፖሊሶች ልብሳቸውን በመቀየር በእግራቸው ወደ ጅንካ ከተማ እየሸሹ ነው።

የፖሊስ ግጭት ወቅታዊ መረጃን በመጥቀስ የኦሞ ህዝቦች ዲሞክራሲያዊ ድርጅት ባወጣው መግለጫ እንደተመለከተው፤ ሐመሮች በወሰዱት የመልሶ ማጥቃት እርምጃ የዞኑን የፖሊስ አዛዥ ሻምበል ለማ አሸናፊን ጨምሮ ሰባት ፖሊሶች ሲገደሉ፤ ስድስት  ፖሊሶች ደግሞ ቁስለኛ ሆነዋል።

ከፖሊሶቹ በተጨማሪ ሁለት ሲቪሎችም መገደላቸውና ሶስት ሰዎች መቁሰላቸው የፖሊስ ሪፖርት ያመለክታል። ፖሊሶችና የዞን መስተዳድር ሰራተኞች ከሐመር አርብቶ አደሮች ይህን ያህል ጥቃት የደረሰባቸው ፤በማጎ ፓርክ  ውስጥ <<የዱር አራዊት ገድላችሁዋል>> ባሏቸው ወጣቶች ላይ  የሀይል እርምጃ በመውሰዳቸው ነው። እንደ ፖሊስ  ወቅታዊ የግጭት ሪፖርት ፣ ጥር 7/2007 ሐሙስ ዕለት በሐመር ወረዳ በ‹‹ላላ›› ቀበሌ በሐመር ብሔረሰብ አርብቶ አደሮችና ፖሊስ መካከል በተፈጠረ ግጭት  የተገደሉት፤- የዞኑ ፖሊስ አዛዥ ሻምበል ለማ አሸናፊ፣ወታደር ሙሴ ማቱሳላ፣ወታደር ደፋሩ ጦና፣ወታደር ካሬ፣ወታደር በኃይሉ፣ስሙ ለግዜዉ ያልታወቀ የልዩ ኃይል ባልደረባ፣ስሟ ለጊዜዉ ያልታወቀ ሴት ባለሙያ እናነመምህር መሳይነሽ መርነህ ናቸው።

ከሟቾቹ በተጨማሪ  የደቡብ ኦሞ ዞን ፍትህ ጸጥታና ደንብ ማስከበር ምክትል ሀላፊአቶ ቹሜሬ የረር፣ ምክትል ሣጅን ጌታሁን ቶላ፣ወታደር ተሰማ መሰረት፣ ወታደር ጌታቸዉ ጻንቃ፣ወታደር ቱላ ኪያ፣ ባሻ ወንድማገኝ ጨነቀ፣ ወታደር ሚልኪያስ ግራኝ፣ወታደር ዘለቀ እና የዞኑ ሴቶችና ሕጻናት መምርያ ሾፌር አቶ ደምሳሽ ሞላ ቆስለው ህክምና እየተከታተሉ ይገኛሉ። በአርብቶአደሩ በኩል ስለደረሰው ጉዳት  እስካሁን መረጃ ለማግኘት አልተቻለም፡፡ አስቀድመው ፖሊሶች እርምጃ እንዲወስዱ ዲመካ ሁነዉ   ትእዛዝ ያሰተላለፉትና ኦፕሬሽኑን ሲመሩ የነበሩት – የሐመር ወረዳ ፍትህ ጸጥታና ደንብ ማስከበር ሃላፊ ኮማንደር ቡራ ካሎ መሆናቸውን ለማወቅ ተችሏል።

ከዞኑ መስተዳድር የወጣ መረጃ እንደሚያመለክተው፤ በነገው ዕለት የዞኑ ሲቪል ሠራተኞች ከስከሬን አንሺ የቀን ሠራተኞችን  ወደ ቦታው  ይዘው በመሄድ አሰከሬኖችን ለማምጣት  የሚንቀሳቀሱ ሲሆን፤ በዚህ ጉዞ ወታደራዊ ኃይል እንዳይኖር ወይም  እንዳያጅባቸው ተወስኗል።

በአሁኑ ሰዓት በሃመር ወረዳ ዋና ከተማ ዲመካ ምንም የፖሊስ ኃይል የሌለ ሲሆን፤ አንዳንድ የወረዳውና ከዞኑ የተንቀሳቀሱ ፖሊሶች የፖሊስ ልብሳቸውን በመቀየር በእግር ጫካ ለጫካ በመጓዝ ወደ ዞኑ ከተማ  ወደ ጂንካ እያቀኑ ሲሆን፤በሽሽት ነፍሳቸውን ያተረፉት ፖሊሶችም የጂንካ ከተማ ነዋሪ፦ ‹‹እንኳን ለቤታችሁ አበቃችሁ›› እያለ እየተቀበላቸው ነው።

ፖሊሶቹም፦ ‹‹ በማናውቀው ነገር አስገብተውን ሊያስጨርሱን ነበር፣ የተፈጠረው ሁኔታ እና በወንድሞቻችን ላይ የደረሰው በእጅጉ አሳዛኝ ነው›› በማለት ቁጭታቸውን እየገለጹ ይገኛሉ ፡፡

የግጭቱን ምክንያቶች በዝርዝር ያስቀመጠው  የኦሞ ህዝቦች ዲሞክራሲያዊ ድርጅት፤መንግስት በግጭቱ ስለደረሰው  አጠቃላይ ጉዳት በቂ መረጃ እንዲሠጥና በድርጊቱ አዛዦችና ፈጻሚዎች ላይ ህጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ፤ በግጭቱ ለተጎዱ ወገኖችና ለደረሰው የንብረት ውድመት ካሳ እንዲከፍል፤ ግጭቱ ከመጪው ምርጫ ጋር በቀጥታ የሚገናኝ ስለሆነ አፋጣኝና አሳታፊ መፍትሄው እንዲፈልግለት፤የፖሊስ ተግባራትና ማኅበራዊ አገልግሎቶች ወደቦታቸው እንዲመለሱ እንዲያደርግ ጠይቋል።

እንዲሁም  ችግሩን ከስሩ ለማስወገድ ሕብረተሰቡን ያሳተፈና በማኅበረሰቡ ተቀባይነት ያለው አካባቢያዊ ዘላቂ መፍትሄ እንዲያበጅና ችግሩ እንዳይባባስና እንዳይስፋፋ አስቸኳይ የማረጋጋት እርምጃ እንዲወስድ የጠየቀው ድርጅቱ፤ የማንአለብኝነት የኃይል እርምጃ መቼውንም መፍትሄ አይሆንምና ፤ለቀጣይም መንግሥት ከዚህ ዓይነቱ አካሄድ እንዲታቀብ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን”ብሏል