ሰላም ባስና ዳሽን ቢራ ከፍተኛ ጉዳት ደረሰባቸው

(ኢሳት ዲሲ–ጥር 3/2010)

በኢትዮጵያ የተከሰተውን ሕዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ በተጠራ አድማና ጥቃት ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰባቸው ሰላም ባስና ዳሽን ቢራ አስታወቁ።

የቢቢሲ የአማርኛው አገልግሎት ያነጋገራቸው የሁለቱ ድርጅቶች ሃላፊዎች እንዳሉት በአድማውና በጥቃቱ ምክንያት ከኪሳራ ባሻገር ህዝቡ በአገልግሎታችን እንዳይጠቀም ከፍተኛ ተጽእኖ ፈጥሯል።

ሰላም ባስ በአራት መስመሮች አገልግሎት ማቋረጡን ሲያሳውቅ ዳሽን ቢራ በተለይ በባህርዳር ከፍተኛ የተቀባይነት ቀውስ እንደገጠመው ገልጿል።

ለቢቢሲ አማርኛ ቃለ መጠይቅ የሰጡት የሰላም ባስ አገልግሎት ማህበር ስራ አስኪያጅ አቶ ሀጎስ አባይ ባለፉት ሁለት ዓመታት በተፈጠረው ችግር ምክንያት ህዝቡ በሰላም ባስ ለመጠቀም ፍራቻ አድሮበታል።

በዚህም ምክንያት የገቢ መቀነስ ታይቷል ሲሉ ገልጸዋል።

በቅርቡ ወደቁልቢ ገብርዔል በመጓዝ ላይ በነበሩ አራት የሰላም ባስ አውቶብሶች ላይ ጥቃት ተሰንዝሮ መስታወቶቻቸው መሰባበሩን አቶ ሀጎስ አስታውሰዋል።

ሁለት የሰላም ባሶች በተለያዩ የሀገሪቱ አከባቢዎች መቃጠላቸውንም ስራ አስኪያጁ ጠቅሰዋል።

ሰላም ባስ በመላ ሀገሪቱ በ17 መስመሮች አገልግሎት እንደሚሰጥ የተናገሩት አቶ ሀጎስ በተፈጠረው የተቃውሞ እንቅስቃሴ ምክንያት የአራቱ መስመሮች አገልግሎት መቋረጡን ገልጸዋል።

በዚህም መሰረት በሀረር፣ ድሬዳዋ፣ ጂጂጋና አሶሳ መስመሮች ሲሰጥ የነበረው አገልግሎት ካለፉት ሶስት ወራት ወዲህ መቋረጡን ለማወቅ ተችሏል።

በሌሎች የሀገሪቱ አካባቢዎች ችግር አልገጠመንም ብለው መናገር ያልደፈሩት አቶ ሀጎስ አባይ ከፍተኛ ተጽዕኖ አልደረሰብንም በሚል አልፈውታል።

በጎንደር ህዝባዊ ተቃውሞ በተቀሰቀሰ ጊዜ በርካታ የሰላም ባስ አውቶብሶች ጥቃት የተሰነዘረባቸው መሆኑ ይታወሳል።

በቅርቡም በወሎ ኡርጌሳና በሰሜን ሸዋ አጣዬ መስመር ተመሳሳይ ጥቃትና እገታ በሰላም ባስ ላይ መደረጉን መዘገባችን የሚታወስ ነው።

ስራ አስኪያጁ አቶ ሀጎስ አባይ በገቢ ደረጃም ጉዳት እንደደረሰባቸው ገልጸዋል።

ከባለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጻር በዘንድሮ ገቢያችን መቀነሱን አውቀናል ብለዋል።

ሰላም ባስ ከኢትዮጵያ ህዝብ በተዘረፈ ገንዘብ የተቋቋመው የትግራይ መልሶ ማቋቋሚያ ድርጅት ኢፈርት ንብረት በመሆኑ በመላ ሀገሪቱ አድማ እንደተጠራበት ይነገራል።

አቶ ሀጎስ ግን ያስተባብላሉ። በአክሲዮን የሚተዳደር ድርጅት ነው በማለት።

በሌላ በኩል በባህርዳር ከተማ በአንድ ቀን ከ60 በላይ ዜጎች በአጋዚ ሰራዊት መገደላቸውን ተከትሎ አድማ የተጠራበት ዳሽን ቢራም ተመሳሳይ ቀውስ እንደገጠመው እየተነገረ ነው።

የፋብሪካው ምክትል ስራአስኪያጅ አቶ ሙሉጌታ ማሩ ለቢቢሲ አማርኛ እንደተናገሩት ዳሽን ቢራ በተለይ በባህርዳር ከፍተኛ ተጽዕኖ ተፈጥሮበታል።

ኪሳራ ባይገጥመንም ከባለፉት ዓመታት ጋር ሲነጻጸር ትርፋችን ቀንሷል ብለዋል አቶ ሙሉጌታ።

ለጥይት መግዣ ገንዘብ አንሰጥም በሚል አገልግሎታችን ላይ አድማ መመታቱ ተገቢ አይደለም ያሉት አቶ ሙሉጌታ እንደሌሎች ድርጅቶች ለመንግስት የምንክፍለው ግብር ብቻ ነው ሲሉም አስተባብለዋል።

በአማራ ክልል ዳሽን ቢራ የሚያዘጋጃቸው የሙዚቃ ዝግጅቶች በተደጋጋሚ አድማ ተመቶባቸው የተቋረጡ መሆኑን መዘገባችን ይታወሳል።

ቢቢሲ አማርኛ ያነጋገራቸው አንድ የባህርዳር ነዋሪ እንዳሉት በባህርዳር ዳሽን ቢራ መጠጣት አደጋ አለው።