ም/ል ጠ/ሚኒስትሩ ተቃውሞ ገጠማቸው

የካቲት ፳፬(ሃያ አራት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የቅዱስ ጊዮርጊስ እና  የአልጀሪያው -ኤል ኡልማ  ቡድኖችን  ጨዋታ ለማየት በባህርዳር ስታዲየም በእንግድነት የተገኙት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስቴር ደመቀ መኮንን ከጨዋታው በፊት ንግግር እንዲያደርጉ በተጋበዙበት ሰአት ጨዋታውን ለመመልከት በስቴዲየሙ የተገኘው ሕዝብ በታላቅ ቁጣ የተቃውሞ ድምጽ በማሰማቱ ንግግራቸውን እንዲያቋርጡ መገደዳቸውን የክልሉ ወኪላችን ገልጻለች፡፡

አብዛኛው ህዝብ ከተቃውሞ ድምጹ ጋር የተቀናቃኝ ፓርቲዎችን የምርጫ ምልክት በእጁ በማሳየት አቶ ደመቀ ንግግራቸውን እንዲያቋርጡ አስገድዷቸዋል፡፡

የጊዮርጊስ ጨዋታ ወደ ባህርዳር የተላለፈው-የህውሃት 40ኛ አመት ዝግጅትን ለማካሄድ ሲባል አዲስ አበባን ከሁሉም ትኩረት ከሚስቡ ነገሮች ነጻ በማድረግ ነዋሪው በሙሉ ልቡ የዕለቱን ዝግጅት በቴሌቪዢን መስኮት እንዲመለከት በማሰብ እንደሆነ ከአዲስ አበባ ቡድናቸውን  ለመደገፍ የመጡ ተመልካቾች ለዘጋቢያችን ገልጸውላታል። በተሰጠው  አስተያየት  ዙሪያ የፌደሬሽኑን አስተያየት  ለማግኘት  ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም።