ማእከላዊ እስር ቤት ተቃዋሚዎችን ሊቀላቀሉ ሲሉ ተያዙ በተባሉ ሰዎች ተጨናንቋል

መጋቢት ፳፪(ሃያ ሁለት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ካለፉት 8 ወራት ጀምሮ በማእከላዊ እስር ቤት ውስጥ የታሰሩት እስረኞች አብዛኞቹ አርበኞች ግንቦት7 ትን ሊቀላቀሉ ሲሉ ተይዘዋል የሚል ክስ ሲመሰረትባቸው እስካሁን ድረስ ክስ ያልተመሰረተባቸው

በርካታ እስረኞች እንደሚገኙ ምንጮች ገልጸዋል።

የሰማያዊ ፓርቲ የአመራር አባላት ከሆኑት ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ፍቅረማርያም አስማማውና እየሩሳሌም ተስፋው እንዲሁም የቀድሞው የአንድነት አመራር አባል የነበረው መሳይ ትኩና ሶስት የድርጅቱ አባላት፣ ከአብርሃ ጅራ፣ መተማ፣ ጎንደር፣ ባህርዳር እና አዲስ አበባ

የመጡ በርካታ ቁጥር ያላቸው ኢትዮጵያውያን በማእከላዊ ታስረዋል።

በአንዳንዶቹ ላይ ለአርበኞች ግንቦት7 ሰዎችን ሲመለምሉና ወደ ኤርትራ ሲልኩ ነበር የሚል ክስ ሲቀርብባቸው፣ አንዳንዶቹ ደግሞ በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞች የአርበኞች ግንቦት7 ትን መረብ ( ኔትወርክ) ሲዘረጉ ነበር የሚል ክስ ቀርቦባቸዋል። ምንጮች እንደሚሉት

አንዳንድ ወታደራዊ ሃላፊዎችም ታስረው ከሚገኙት መካከል ናቸው። ቀድሞ ብሎ ከጋምቤላ ተይዘው የመጡት እስረኞች በማእከላዊ ከፍተኛውን ቁጥር ይዘው የነበሩ ቢሆንም፣ በአሁኑ ሰአት ከአርበኞች ግንቦት7 ጋር በተያያዘ እየታፈሰ የሚገቡት ሰዎች ማእከላዊን አጣበውታል።

የአየር ሃይል አባላት የሆኑት ዳንኤል ግርማ ፣ ማስረሻ ሰጠኝ፣ ገዛሃኝ ደረሰ እና ብሩክ አጥናባቸው በማእከላዊ እስር ቤት ውስጥ በከፍተኛ ሁኔታ ተደብድበዋል። ስማቸውን እስካሁን በትክክል ለማወቅ ባይቻልም፣ ከአብርሃ ጅራ አካባቢ የተያዙት አንድ የኢህአዴግ ወታደር

አመራር ከፍተኛ ድብደባ ተፈጽሞበት ማእከላዊ ታስሯል። በቅርቡ ከዚሁ አካባቢ አርበኞች ግንቦት7ትን መንገድ መርተው ወደከተማ አስገብተዋል ተብለው የተያዙት ወደ ማእከላዊ ተዛውረዋል። ቀድሞ ብሎ የአብርሃ ጅራ የአንድነት ፓርቲ  አመራር አባላት አንጋው ተገኝ፣

አባይ ዘውዱና ሌሎችም ተመሳሳይ የሽብር ክስ ተመስርቶባቸዋል።

መንግስት በሰሜን የአገሪቱ ክፍል ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሰራዊት አሰማርቶ እንደሚገኝ መዘገባችን ይታወቃል። አሁን እንደ አዲስ የተጧጧፈው ዘመቻም በአካባቢው የሚታየው ውጥረት የፈጠረው ሊሆን እንደሚችል ምንጮች ያክላሉ።

ታዋቂው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣ የቀድሞው የአንድነት  አመራሪዎች አንዱአለም አራጌና ናትናኤል መኮንን፣ የመኢዴፓው ክንፈሚካኤል ደበበ ( አበበ ቀስቶ)፣ የሽዋስ አሰፋ፣ ሃብታሙ አያሌው፣ ዳንኤል ሽበሺ እና ሌሎችም ታዋቂ ፖለቲከኞች ከግንቦት7 ጋር ሲሰሩ

ተገኝተዋል የሚል ክስ ተመስርቶባቸው በእስር ላይ መሆናቸው ይታወቃል።