ማእከላዊ አፍሪካን ሪፑብሊክን በማሸነፍ የኢትዮጵያን ታሪክ እንደምንቀይረው አልጠራጠርም ሲል ምንያህል ተሾመ ተናገረ

ሰኔ ፲፪ (አስራ ሁለት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:- ምን ያህል ለኢሳት እንደገለጸው በተፈጠረው ነገር በእጅጉ አዝኗል። እኔ በአገሬ ላይ አውቄ እንዲህ አይነት ነገር አልሰራም ያለው ምንያህል፣ ቢጫ ካርድ ከተሰጠው ከ10 ወራት በሁዋላ ብዙ ጨዋታዎችን መጫወቱ ቢጫ ማግኘቱን እንዲዘነጋ እንዳደረገው  ገልጿል።

የሚመለከታቸው የስፖርቱ ሀላፊዎች “ሁለት ቢጫ ካርዶችን ማየትክን  አልነገሩህም ነበር? ተብሎ ለተጠየቀው ደግሞ  አንድ ቢጫ ብቻ እንዳለኝና ከደቡብ አፍሪካ ጋር በማደርገው ጨዋታ እንድጠነቀቅ ተነግሮኝ ነበር፣ ከዚያ ውጭ ግን ማንም ሁለት ቢጫ ካርድ አይተሀልና አትጫወትም ያለኝ የለም በማለት መልሷል።

የደቡብ አፍሪካ የመገናኛ ብዙሀን በኢትዮጵያ ላይ 6 ነጥብ እንዲቀነስ የሚያደርጉት ውትወታ የህግ ድጋፍ የሌለው ነው በማለት የሚናገረው ምንያህል፣ ቡድናችን አሁን ባለው አቋሙ ማእከላዊ አፍሪካንም ሆነ ሌላ ጠንካራ ቡድን በማሸነፍ የኢትዮጵያን ታሪክ እንደሚቀይር አምናለሁ ሲል እምነቱን ገልጿል።