ሙስሊም ኢትዮጵያውያን ከፍተኛ ተቃውሞ አሰሙ

መጋቢት ፲፰ (አስራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ላለፉት ሁለት አመታት ሲካሄድ የቆየው፣ ከቅርብ ወራት ወዲህ ቀዝቀዝ ብሎ የነበረው የሙስሊም ኢትዮጵያውያን ተቃውሞ ዛሬ ቁጥሩ እጅግ ብዙ የሆነ ሙስሊም ኢትዮጵያውያን በተገኙበት በአንዋር መስጊድ ተካሂዷል።

ሙስሊም ኢትዮጵያዊያኑ   አላህ ሰላምን እንዲያመጣ ሲማጸኑ አርፍደዋል። የሰላም ሰዎች መሆናቸውን ነጭ ወረቀቶችን በማውለብለብ ያሳዩ ሲሆን ተቃውሞውም ያለምንም የጸጥታ ችግር ተጠናቋል።

መንግስት እንቅስቃሴውን በሃይል እንደተቆጣጠረው ሲያውጅ ቢከርምም ፣ ዛሬ በአንዋር የተገኘው ህዝብ ብዛት ሙስሊሙ ኢትዮጵያዊ ጥያቄዎቹ ካልተመለሱ ዝም የማይል መሆኑን አሳይቷል ሲል አንድ ስሙ እንዳይገለጽ የፈለገ ወጣት ለዚጋቢያችን ተናግሯል።

የዛሬው ተቃውሞ በግፍ እስር ላይ ለሚገኙት ለመፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት የስነልቦና ጥንካሬ ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርግ የገለጸው አስተያየት ሰጪ፣ በኮሚቴ አባላቱ ላይ የሚሰጠው የሀሰት የፍርድ ውሳኔም ተቃውሞውን ይበልጥ ያጎላዋል እንጅ አያደበዝዘውም ብሎአል። የመፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ  አባላት የፍርድ ሂደት ነጻና ገለልተኛ አይደለም በሚል በአለማቀፍ የሰብአዊ መብት ድርጅቶች ይተቻል።