ሙስሊም ኢትዮጵያውያን ለመሪዎቻቸው አጋርነታቸውን በተቃውሞ ሊገልጹ ነው

ሚያዚያ ፩ (አንድ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የቀረባባቸውን ክስ በፍርድ ቤት እየተከራከሩ የሚገኙት  የሙስሊሙ የመፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት በፍርድ ሂደቱ ላይ ያቀረቡት መከራከሪያና ያሳዩት ጥንካሬ  የመላውን ሙስሊም ማህበረሰብ ቀልብ በሳበበት በዚህ ወቅት፣ ሙስሊሙ ማህበረሰብ ለመሪዎቹ ያለውን ድጋፍ ለመግለጽና የመንግስት ህገወጥ እርምጃ ለመቃወም የፊታችን አርብ የተቃውሞ ድምጹን እንደሚያሰማ ታውቋል።

የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት በእስር ቤት ውስጥ እጅግ አሰቃቂ ሆነ ድብደባና ማሰቃየት ደርሶባቸዋል። አንዳንዶች እስከ 2 ሺ የሚደርስ ቁጭ ብድግ  ስፖርት እንዲሰሩ ታዘዋል። ሌሎች ደግሞ ብልቶቻቸውን ተመትተዋል። አንዳንዶች ጺማቸው እየተነጨ ሲደበደቡ ሌሎች ደግሞ በርሃብ ተቀጥተዋል። መሪዎቹ በዳኞች ጫና የተነሳ እንደልባቸው መናገር ባለመቻላቸው እንጅ የደረሰባቸውን ግፍ እስካሁን ካቀረቡትም በላይ ለማቅረብ እንደሚችሉ ችሎቱን የሚከታተሉ ወገኖች ይገልጻሉ።