ሙስሊም ኢትዮጵያውን በአገር ውስጥ ለሚካሄደው የሙስሊሙ እንቅስቃሴ ድጋፋቸውን ገለጡ::

ነሀሴ ፳፪ (ሀያ ሁለት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:- በቤልጂየም እና በሆላንድ የሚኖሩ ሙስሊም ኢትዮጵያውን በአገር ውስጥ ለሚካሄደው የሙስሊሙ እንቅስቃሴ ድጋፋቸውን ገለጡ::

 

ሙስሊም ኢትዮጵያውያኑ ይህን የገለጡት ባለፈው ቅዳሜ በቤልጂየም ዋና ከተማ ብራሰልስ ፣ የኢድ አል ፈጥርን በአል ምክንያት በማድረግ ባዘጋጁት ዝግጅት ላይ ነው።

 

የኢትዮጵያውያን ቤልጂየማውያን ሙስሊሞች መሀበር ሉቅማን መሪ የሆኑት አቶ አብየ ያሲን ሙስሊም ኢትዮጵያውያን ለላፉት 9 ወራት ለመብታቸው መከበር ያደረጉትን እንቅስቃሴ፣ ከአጀማመሩ አሁን እስካለበት ሂደት በዝርዝር አቅርበዋል።

 

አቶ አብየ ሙስሊሙ ማህበረሰብ ያቀረባቸው ሶስት ጥያቄዎች ለመመለስ ቀላል ቢሆኑም ፣ ከአብዮታዊ ዲሞክራሲ አስተሳሰብ ውጭ ሌላ አመለካከት ለመቀበል ፈቃደኛ የማይሆነው ኢህአዴግ አገዛዝ ጥያቄዎችን ለመመለስ ፈቃደኛ አለመሆኑን ገልጠዋል።

 

በክርስቲያኑ በኩል በተለይም በውጭ አገር የሚገኘው ሲኖዶስ ለሙስሊሙ እንቅስቃሴ ያሳየው ድጋፍ የሚመሰገን ቢሆንም፣ መላውን የኢትዮጵያ ህዝብ ከጎን በማሰለፍ የእንቅስቃሴውን አድማስ ለማስፋት ብዙ ስራ እንደሚጠብቅ ተናግረዋል።

 

በዝግጅቱ ላይ ለሙስሊሙ እንቅስቃሴ የተለየ ድጋፍ ላደረጉ ድርጅቶች የማበረታቻ የመስክር ወረቀት ተሰጥቷል።

 

የኢትዮጵያ ሰታላይት ቴሌቪዥን ኢሳት በአገር ውስጥ ካሉ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች፣ በውጭ ከሚገኙት አየልጀዚራ አረብኛ ክፍል፣ ከሬዲዮ ደግሞ ቢላል ሬዲዮ የክብር ሰርተፊኬት ከተበረከተላቸው መካከል ይገኙበታል።

ዝግጅቱን ሉቅማን የኢትዮጵያውያን ቤልጀማውያን ሙስሊሞች ማህበር እና በኔዘርላንድስ የሚገኘው ሰንሰሌት ፋውንዴሽን በጋር ያዘጋጁት ነው።

 

____________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide