መድረክ በአዲሱ የከተማ ቦታ ሊዝ አዋጅ ላይ ከህዝብ ጋር ለመወያየት ስብሰባ ጠራ

መጋቢት 17 ቀን 2004 ዓ/ም
ኢሳት ዜና:- መድረክ በቅርቡ የወጣውን የመሬት ሊዝ አዋጅ በመቃወም መጋቢት 22 ቀን 2004 ዓም በጎተራ አካባቢ በሚያደርገው ስብሰባ በመጀመሪያው የውይይት ወቅት ከተገኘው ህዝብ በላይ ይገኛል ብሎ እንደሚጠብቅ ጽህፈት ቤቱ ገልጧል። በሙገር ስሚንቶ አንተርፕራይዝ መሰብሰቢያ አዳራሽ በሚካሄደው ስብሰባ የሊዝ አዋጁ በህብረተሰቡ ህይወት ላይ ያለው ተጽእኖ ይዳሰሳል።
በመላ አገሪቱ ከፍተኛ ተቃውሞ የገጠመው አዲሱ የመሬት ሊዝ አዋጅ ከዚህ ወር ጀምሮ በደቡብ ተግባራዊ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።
የደቡብ ክልል አዋጁን በመተግበር በኩል ቀዳሚ ይሆናል። በአማራ እና በትግራይ ክልሎች አዋጁን በተመለከተ ምንም አይነት ውይይት ተደርጎ አያውቅም።