መንግስት ትችቶችን ወደ ሁዋላ በማለት ተጨማሪ መሬቶችን ለውጭ ባለሀብቶች ለመስጠት ማቀዱ ታወቀ

ሚያዚያ ፲፪ (አስራ  ሁለት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ኢትዮጵያዊያን ገበሬዎችን በማፈናቀል ለሃገር ውስጥና ለውጪ ባለሃብቶች ሰፋፊ መሬቶችን በማቅረቡ ከፍተኛ ተቃውሞ
እየቀረበበት ያለው የኢትዮጽያ መንግስት ይህንኑ ተግባሩን በማጠናከር ሰፋፊ የእርሻ መሬቶች የያዘ ዞን ከማቋቋም
በተጨማሪም የግብርና ኢንቨስትመንትን ብቻውን የሚመራ ራሱን የቻለ ተቋም ለመመስረት ማቀዱን ከግብርና ሚኒስቴር
የተገኘ ሪፖርት አመለከተ፡፡
የግብርና ኢንቨስትመንትን በፍጥነት እና በተቀናጀ ሁኔታ ለማስፋፋትና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳውን ለማጎልበት እንዲቻል
የግብርና ኢኮኖሚ ዞን ለመገንባት በተያዘው ዕቅድ መሰረት በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል 100,000 ሄክታር
፣በጋምቤላ 67,000 ሄክታር እንዲሁም በደቡብ ክልል 118,000 ሄክታር መሬት የመለየት ሥራ በማከናወን
ዝርዝር የአዋጪነትና የተስማሚነት ጥናት መካሄዱን ሪፖርቱ ይጠቁማል፡፡በዚህ መሰረት የግብርና ኢኮኖሚ ዞን ሊደራጅ
የሚችልበት አግባብና አማራጮችን አጠናክሮ መቀጠል እንዲቻል አሁን ያለውን ተቋማዊ አቅም ማጠናከር አስፈላጊ ሆኖ
በመገኘቱ የግብርና ኢንቨስትመንትን ስራን የሚያስተባብርና የሚደግፍ ተቋም በማቋቋም ሂደት ላይ መሆኑን ጠቁሟል፡፡
በያዝነው የኢትዮጽያዊያን 2005 በጀት ዓመት ስድስት ወራት ብቻ በግብርና ኢንቨስትመንት የባለሃብቶችን ድርሻ
ለማስፋት በማቀድ በሶማሌ ክልል 2,000 ሄክታር፣በኦሮሚያ 90 ሄክታር መሬት በመለየት ወደመሬት ባንክ ገብቶ
ለባለሃብቶች እንዲከፋፈል መደረጉን የሚኒስቴሩ ሪፖርት ስኬት ነው ሲል አስቀምጦታል፡፡
ከመሬት መቀራመት ጋር በተያያዘ የአነስተኛ ገበሬዎችንና የምግባረ ሰናይ ድርጅቶችን ተደጋጋሚ የቅሬታ አቤቱታ ጆሮ
ዳባ ልበስ ያለው የኢትዮጽያ መንግስት በግብርና ዘርፍ የተሰማሩ ባለሃብቶች ያሉባቸውን ችግሮች ለመፍታት
መንቀሳቀሱን በሪፖርቱ ጠቅሶአል፡፡በዚሁ መሰረት በግብርና ኢንቨስትመንት የተሳተፉ ባለሃብቶች በገቡት ውል መሰረት
መሬት አጠቃቀማቸውን እንዲያሻሽሉ በመገምገም ድጋፍ ለማድረግ በተያዘው ዕቅድ መሰረት ከሐምሌ 1/2004 እስከ
ታህሳስ 30/2005 ባሉት ጊዜያት ብቻ በቤንሻንጉል ጉሙዝና ጋምቤላ ክልሎች ለተሰማሩ 303 ባለሃብቶች ድጋፍ
መሰጠቱን አስታውቋል፡፡