ለጋዜጠኛ ኤፍሬም በየነ ህክምና የሚውል የእራት ግብዣ ተዘጋጀ

(ስድስት)ቀን ፳፻፮ /  ኢሳት ዜና :-በቀረረበባቸው የፕሬስ ክስ ወደ አዋሳ በተጉዋዙበት ወቅት በድንገት በተከሰተ የተሸከርካሪ አደጋ ከፍተኛ ጉዳት የደረሰበትን የኢትዮ ምህዳር ጋዜጣ  አዘጋጅ ለሆነው ለወጣት ኤፍሬም በየነ የሕክምና ወጪ የሚውል የገቢ ማሰባሰቢያ የእራት ምሽት ሰኞና ማክሰኞ በአዲስአበባ እንደሚካሄድ ከዕርዳታ አስተባባሪዎች መካከል አንዱ ለሪፖርተራችን ገልጿል፡፡

በዚህ የእራት ምሽት ላይ 500 ብር ዋጋ ያላቸው ትኬቶች ተዘጋጅተው በመሸጥ ላይ ሲሆኑ በተለይ ጋዜጠኞች ትኬቱን በመሸጥና በግዥ በመሳተፍ ከፍተኛ ድጋፍ እያደረጉ መሆናቸው ታውቆአል፡፡

በአዲስአበባ በአትላስ ሆቴል አካባቢ የሚገኘው ካናዳ ካፌ፣ባር እና ሬስቶራንት የእራት ፕሮግራሙን ስፖንሰር ያደረገ መሆኑ የታወቀ ሲሆን ከዚህ ዝግጅት ከ80ሺ ብር በላይ ገቢ ይሰበሰባል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

የ27 ዓመቱ ጋዜጠኛ ኤፍሬም በደረሰበት ጉዳት በማጅራቱ አካባቢ የአከርካሪ አጥንቱ የተጎዳ ሲሆን በሳምባው ላይ የተከሰተው ሕመም እያገገመ መሆኑን ባለፈው ቅዳሜ  ከወጣው ከአዲስአድማስ ጋዜጣ ጋር ባደረገው ቃለምልልስ አስታውቆአል፡፡

ጋዜጠኛ ኤፍሬም ለጊዜው በኮርያ ሆስፒታል እየተረዳ ቢሆንም በዘላቂነት ለማገገም የውጪ አገር ከፍተኛ ሕክምና እንደሚስፈልገው በሕክምና ባለሙያዎች እንደታመነበት አስተባባሪው አስታውሶአል፡፡