ሂውመን ራይትስ ወች በሙስሊሙ ላይ የሚደርሰውን በደል አወገዘ

(Aug. 15) የኢትዮጵያ መንግስት አፍሶ ያሰራቸውን 17 የሙስሊም መሀበረሰብ መሪዎች በአስቸኳይ እንዲፈታ ሂውማን ራይትስ ዎች ጠየቀ። የታሰሩ ሙስሊሞች ላይ አስገድዶ መድፈርና ድብደባ መፈጸሙን አወገዘ።
በአዲስ አበባና በሌሎች ከተሞች ሲካሄድ በነበረው የሙስሊሙ ማሀበረሰብ ሰላማዊ የመብት ጥያቄ ሲያስተባብሩ የነበሩ እኒህ 17 መሪዎች ጠበቃ የማናገር መብታቸው ታግዶ ከሶስት ሳምንታት በላይ መታሰራቸው ኢፍትሀዊ መሆኑን ሂውማን ራይት ዎች በመግለጫው አስታውቋል።
ከጁላይ 13 ጀምሮ በሰላማዊ መንገድ የመብት ጥያቄ ሲያነሱ የነበሩትን የሙስሊሙ እምነት ተከታዮችን፤ የፌደራል ፖሊስና የጸጥታ ሀይሎች ሲያዋክቡ፡ ሲደበድቡ፡ እንዲሁም አፍሰው ሲያስሩ መቆታቸውን የገለጸው ሂውማን ራይት ዎች መግለጫ፤ በርካቶቹ ቢለቀቁም በእስር ቤት በነበሩበት ግዜ ያለአግባብ እንግልት ደርሶባቸዋል።
ከጁላይ 19 እስከ 21 ባሉት ቀናት የታሰሩት የሙስሊም መሪዎች ግን እስካሁንም በእስርላይ እንደሚገኙ ገልጧል።
የኢትዮጵያ መንግስት የሙስሊም ዜጎቹን ጥያቄ በውይይት እንጂ በብጥብጥና በሀይል ለመፍታት መሞከሩ ሃለፊነት የጎደለው ተግባር ነው ሲል የሁውመን ራይትስ ወች የአፍሪካ አህጉር ቀደምት ተመራማሪ ቢን ለውረንስ ተችተዋል።
የጸጥታ ሀይሎችም ህጉን ማስከበር እንጂ ህጉን መናድ የለባቸውም ሲሉ ተናግረዋል፤ ቢን ላውረንስ። የሂውመን ራይትስ ወች፤ ይህ መግለጫ መንግስት የሙስሊሙን ማህበረሰብ ላይ ያደረሰውና እያደረሰ ያለው ኢፍትሀዊ እርምጃ፤ ሙስሊሙ ማህበረሰብ ህገመንግስቱን በመጣስ በሀይማኖታቸን ጣልቃ መግባቱን ያቁም የሚል ጥያቄ በማንሳታቸው መሆኑን ጠቅሷል።
ይህንን ችግር ከመንግስት ጋር በመነጋገር ለመፍታት፤ ከሙስሊሙ ማህበረሰብ የተወጣጣ ኮሚቴ ባለፈው ጥር መቋቋሙን ያስታወሰው የሂውማን ራይትስ ወች፤ ከኮሚቴ አባላቱ መሀከል ሰባቱ ከሌሎች ዘጠኝ የሀይማኖት መሪዎችና አክቲቪስቶች እንዲሁም አንድ ጋዜጠኛ መንግስት ማሰሩን አስታውቋል።
የሂውመን ራይትስ ወች መግለጫ በኮለፌ ቀራንዮ በፌደራል ፖሊሶች ከተያዙት መሀከል ሁለት ሴቶች ሂጃባቸውን ወይም የእራስ መከናነቢያቸውን በሀይል ማስወለቃቸውን፤ አላወልቅም ባሉት ላይ ምራቃቸውን ፊታቸው ላይ መትፋታቸውን፤ እንዲሁም ሌላ ሙስሊም ሴትን በእስር ቤት እያከለች መድፈራቸውን የአይን ምስክሮችን ጠቅሶ አሳፍሯል። ድርጊቱንም አውግዟል።
በእስር ላይ የነበሩ በርካቶች በፖሊስ ቆመጥ መደብደባቸውና ወከባና እንግልት መቀበላቸውን ሂውመን ራይትስ ወች የገለጸ ሲሆን፤ በሙስሊሙ ኮሚቴ አመራር አባላትና የሀይማኖት አባቶችም ላይ ድብደባ እንደደረሰባቸው አስታውቋል።
የሙስሊሞች ጉዳይ የተባለው ጋዜጣ አዘጋጅ የሆኑ ሁለት የቤተሰብ አባላት፤ አክመል ነጋሽና ኢሳክ እሸቱ፤ በትንሹ ለ10 ቀናት ያህል በቁም እስር ላይ እንደነበሩ ያመለከተው የሂውማን ራይትስ ወች መግለጫ የፌደራል ፖሊስ የበርካታ የሙስሊም መሪዎች አክቲቪስት ጋዜጠኞችን ቤት በማሰስ ላይ እንደነበርም ገልጿል።