የማሌዢያ ጠቅላይ ሚኒስትር በእድሜ ረጅሙ መሪ ሆኑ

(ኢሳት ዲሲ–ግንቦት 2/2010) በጡረታ ተገለው የነበሩት የቀድሞ የማሌዢያ ጠቅላይ ሚኒስትር በድጋሚ የሃገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው ተመረጡ።

ከ15 አመት በኋላ ወደ ጠቅላይ ሚኒስትርነቱ መንበር የተመለሱት ሞሃታሂር ሞሃመድ የአለም የመጀመሪያው የእድሜ ባለጸጋው የሃገር መሪ ሆነዋል።

እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2003 በጡረታ የተገለሉትና የ92 አመት የእድሜ ባለጸጋው ሞሃታሂር የፓርላማውን 113 መቀመጫ በማግኘት ማሸነፋቸው ደግሞ ሌላ አነጋጋሪ ጉዳይ ሆኗል።

ከ2 አስርት አመታት በኋላ ማሌዢያ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትሯን በድጋሚ መሪዋ  አድርጋ መርጣለች።

ከሁለት አስርት አመታት በፊት ሞሃታሂር ሞሃመድ ማሌዢያን ሲመሩ ሃገራቸውን የኢሲያ ሃገራት ነብር የሚል ስያሜ እንዲሰጣት አድርገው እንደነበር መረጃዎች ያመለክታሉ።

በሌላ በኩል ደግሞ ለ22 አመታት ሃገሪቱን መርተው የነበሩት ሞሃታሂር ተቀናቃኞቻቸውን በማሰቃየትና በሌሎች ተግባሮቻቸው ጨካኝ መሪ ናቸው ይባላሉ።

ነገር ግን ሞሃታሂር የሀገራቸውን ኢኮኖሚ በማሳደጉ በኩል ያደረጉት አስተዋጽኦ ግን ጥሩ ዝናን እንዲያተርፉ እንዳደረጋቸው ይነገራል።

በጠቅላይ ሚኒስትርነት ያገለገሉትና በጡረታ ተገለው የነበሩት የ92 አመት እድሜ ባለጸጋው ሞሃታሂር በድጋሚ በተቀናቃኝነት ወደ ስልጣን ፉክክሩ ሲመጡ ማንም ያሸንፋሉ ብሎ አልጠበቀም ነበር ።

ሞሃታሂር ሞሃመድ በድጋሚ መመረጣቸው አነጋጋሪ ሆኗል።

ነገር ግን በእድሜ ቀዳሚው በመባል ዝናን የተጎናጸፉት ሞሃታሂር ከ222 መቀመጫዎች 113ቱን በማግኘት አሸናፊነታቸውን አረጋግጠዋል።

የጠቅላይ ሚኒስትርነቱንም ቦታ ቃለ መሃላ ፈጽመዋል።

ከ15 አመት በኋላ ወደ ስልጣን የተመለሱት ሞሃታሂር በዚህ ምርጫ ሰላማዊ ፉክክር በመድርግና የሕዝብን ድጋፍ በማግኘት ማሸነፋቸው ክስተቱን አስደናቂ አድርጎታል ብሏል ቢቢሲ በዘገባው።

የእድሜ ባለጸጋው ሞሃታሂር ወደ ስልጣን መምጣት ምናልባትም በሃገሪቱ እየናረ የመጣውን የኑሮ ውድነትና የኢኮኖሚ ቀውስ ብሎም ሙስናን በመዋጋቱ ረገድ የተሻለ ነገር ሊያመጡ ይችላሉ የሚል ተስፋ ተጥሎባቸዋል።

ሞሃታሂር በአለም የመጀመሪያውና ትልቁ የእድሜ ባለጸጋ በመሆን የመሪነት መንበሩን ተረክበዋል።