በምስራቅ ጉጂ ዞን የሚካሄደው ተቃውሞ ቀጥሎአል

በምስራቅ ጉጂ ዞን የሚካሄደው ተቃውሞ ቀጥሎአል
(ኢሳት ዜና ሚያዝያ 29 ቀን 2010 ዓ/ም) ሚድሮክ ኢትዮጵያ በሻኪሶና አካባቢው የወርቅ ማእድን ማውጣት ስራውን ለተጨማሪ 10 አመታት እንዲቀጥል የፈቃድ እድሳት ማግኘቱን ተከትሎ በሻኪሶና አካባቢው የተጀመረው ተቃውሞ ዛሬም ቀጥሎ ውሎአል።
የአካባቢው ነዋሪዎች እንደሚገልጹት በለገንደቢ፣ አዶላና ሌሎችም አካባቢዎች ህዝቡ እስከ እኩለቀን ድረስ ተቃውሞውን ሲያሰማ የዋለ ሲሆን፣ ከሰዓት በሁዋላ የንግድ ድርጅቶችን በመዝጋት ተቃውሞውን እየገለጸ ነው።
ትናንት አዲሱ የመከላከያ ሚኒስትር አቶ ሞቱማ መቃሳ ወደ አካባቢው ተጉዘው ህዝቡን ያነጋገሩ ሲሆን፣ ከክልሉ ፕሬዚዳንት አቶ ለማ መገርሳ ጋር ተነጋግረው አስቸኳይ መፍትሄ እንደሚሰጡ ሲገልጹ፣ ተሰብሳቢው ባለመደሰት ስብሰባውን እያቋራጠ መውጣቱን የአካባቢው ነዋሪዎች ተናግረዋል።
የሚድሮክ መኪኖች ዛሬ ጠዋት ላይ ዘወትር እንደሚያደርጉት ሰራተኞችን ወደ ለገደንቢ አለመውሰዳቸውን ምንጮች አክለው ገልጸዋል።
እስከአሁን በተደረገው ተቃውሞ የተወሰኑ ሰዎች ቢታሰሩም፣ የሞቱ ሰዎች እንደሌሉ ነዋሪዎች አክለው ገልጸዋል።