የኬንያ አንድ የሀገሪቱ የምርጫ ኮሚሽን ከፍተኛ ባለስልጣን ከሀገር ኮበለሉ

(ኢሳት ዜና–ጥቅምት 8/2010) በኬንያ አንድ የሀገሪቱ የምርጫ ኮሚሽን ከፍተኛ ባለስልጣን በደረሰባቸው የግድያ ዛቻ ምክንያት ወደ አሜሪካ መኮብለላቸው ተሰማ።

የከፍተኛ ባለስልጣኗ ከሀገር መኮብለል በድጋሚ በሀገሪቱ ሊካሄድ በዝግጅት ላይ ያለውን ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ተአማኒነትን ጥርጣሬ ውስጥ መክተቱ ታውቋል።

በሌላ ዜና በላይቤሪያ የተካሄደው ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ተወዳዳሪዎቹ በቂ ድምጽ ማግኘት አልቻሉም በሚል ምርጫው በድጋሚ እንዲካሄድ ተወስኗል።

በኬንያ የሚካሄደው የድጋሚ ምርጫ በሚቀጥለው ሳምንት ለማካሄድ ዝግጅት እየተደረገ ባለበት ወቅት አንድ የሀገሪቱ የምርጫ ኮሚሽን ከፍተኛ አባል በደረሰባቸው የግድያ ዛቻ ምክንያት ወደ አሜሪካ ሸሽተዋል።

ሮዝሊን አኮሞቤ ከኒዮርክ ከቢቢሲ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ የምርጫ ኮሚሽኑ የፖለቲካ አጣብቂኝ ውስጥ መግባቱንና ምንም አይነት ውሳኔ መወሰን የማይችልበት ሁኔታ ውስጥ መሆኑን ተናግረዋል።

በሳቸው ላይ የግድያ ዛቻ እየተደረገ ባለበትና ባላፈው ነሀሴ የምርጫ ኮሚሽኑ የኢንፎርሜሽኝ ቴክኖሎጂ ሃላፊው በተገደሉበት ሁኔታ ውስጥ በሀገር ውስጥ መቆየታቸው በራሳቸው ሕይወት ላይ እንደመፍረድ የሚቆጠር ነው ብለዋል።

በሀገሬ እየኖርኩ እንዲህ አይነት ፍርሃት ተሰምቶኝ አያውቅም ሲሉ አክለዋል።

የምርጫ ኮሚሽኑ ወይዘሮዋ ከስራቸው በመልቀቃቸው ሀዘን ተሰምቶኛል ሲል የኮሚሽኑ ሊቀመንበር ደግሞ አሁን ኮሚሽኑ ባለበት ሁኔታ ተአማኒነት ያለው ምርጫ ይካሄዳል ብለው ማረጋገጫ መስጠት እንደማይችሉ ተናግረዋል።

የተቃዋሚው መሪ ራይላ ኦዲንጋ ባለፈው ሳምንት ከምርጫው ራሳቸውን ማግለላቸውን ቢያሳውቁም የምርጫ ኮሚሽኑ ግን ስማቸውን በምርጫ ወረቀቶች ላይ እንደሚያኖር ገልጿል።

ከሚሽኑ ምክንያቱን ሲያስቀምጥም ኦዲንጋ ከምርጫው መገለላቸውን በሕጋዊ ፎርም ላይ አልሞሉም ብሏል።

ባለፈው ነሀሴ በተደረገው ምርጫ የወቅቱ ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ ማሸነፋቸው ይፋ ከተደረገ በኋላ ተቃዋሚው ኦዲንጋ ማጭበርበር ተፈጽሟል ሲሉ ቅሬታ ካቀረቡ በኋላ የምርጫ ኮሚሽኑ ባደረገው ማጣራት አረጋግጦ የድጋሚ ምርጫ እንዲደረግ መወሰኑ ይታወሳል።

ከባለፈው ነሀሴ ወር ወዲህ ምርጫውን ተከትሎ በተፈጠረው ረብሻ እስካሁን 70 ሰዎች ሲሞቱ ከዚህ ውስጥ 33 የሚሆኑት በመዲናይቱ ናይሮቢ መሞታቸው ታውቋል።

በሚቀጥለው ሳምንት በሚደረገው ምርጫም ከፍተኛ ብጥብጥ ይነሳል የሚል ፍራቻ ነግሷል።

በሌላ ዜና በላይቤሪያ ባለፈው ማክሰኞ በተደረገው ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ የቀድሞው ታዋቂ የእግር ኳስ ተጫዋች ጆርጅ ዊሃ ከተፎካካሪው ከምክትል ፕሬዝዳንቱ ጆሴፍ ቦአካይ የበለጠ ድምጽ አግኝቶ ነበር።

ነገር ግን ምርጫውን ለማሸነፍ ከ50 በመቶ በላይ ድምጽ አስፈላጊ በመሆኑ በሁለት ሳምንት ውስጥ ሌላ ምርጫ ይካሄዳል ተብሎ ይጠበቃል።

ጆርጅ ዊሃ 39 በመቶ ድምጽ ሲያገኝ ጆሴፍ ቦአካይ ደግሞ 29 በመቶ አግኝተዋል።

አሸናፊው ሀገሪቱን ለ12 አመታት ያስተዳደሩትንና የኖቤል የሰላም ተሸላሚ የሆኑትን ኤለን ጆንሰን ሰርሊፍን ይተካል።

የአህጉሪቱ የመጀመሪያዋ ሴት መሪ የሆኑት ሰርሊፍ ላይቤሪያ ከረጅም አመታት የእርስ በርስ ጦርነት ወጥታ ወደ ሰላምና መረጋጋት እንድታመራ አስተዋጽኦ በማድረጋቸው ይታወቃሉ።