የአባይ ወንዝ ከ25 ሔክታር በላይ በእምቦጭ አረም መወረሩ ተገለጸ

(ኢሳት ዜና–መስከረም 10/2010) የአባይ ወንዝ ከ25 ሔክታር በላይ በእምቦጭ አረም መወረሩ አስደንጋጭ እንደሆነባቸው የባህርዳር ነዋሪዎች ገለጹ።

አረሙን ለመከራከል ደግሞ የፌደራል መንግስቱ የሚጠበቀውን ያህል ምላሽ አለመስጠቱ ችግሩ እየተባባሰ እንዲመጣ አድርጎታል ይላሉ።

ከጣና ሃይቅ አልፎ በመሄድ የአባይ ወንዝን እየወረረ ያለውን የእምቦጭ አረም ለመከላከል የፌደራል መንግስቱ የሚጠበቅበትን እንዳልሰራ በአማራ ክልላዊ መንግስት ባለስልጣናት የቀረበውን ቅሬታ ተከትሎ የኢሳት ወኪሎች ያናገሯቸው የባህርዳር ነዋሪዎች የተሰማቸውን ሀዘን ገልጸዋል።

የባህርዳር ኢሳት ወኪሎች ተዘዋውረው ካናገሯቸው መካከል በቱሪዝም አስጎብኝነት የተሰማሩትና ስማቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁት ግለሰብ የባህርዳር ከተማ መስተዳድር የአባይ ወንዝ ከ25 ሄክታር በላይ በእምቦጭ አረም እንደተወረረ ይፋ ማድረጉ ተገቢ ነው ብለዋል።

ሆኖም ግን ለዚህ የድረሱልኝ ጥሪ የፌደራል መንግስቱ ምላሽ አለመስጠቱ በሀገሪቱ ውስጥ ኢፍትሃዊነት እንደሰፈነና እኩልነት እንደሌለ የሚያመላክት ነው ብለዋል።

አያይዘውም ከጣና ሀይቅ ተሻግሮ በአባይ ወንዝ ላይ እየተስፋፋ የሄደው አረም የቱሪስት የስራ ዘርፉን ክፉኛ በመጉዳቱ ከፍተኛ ችግር ላይ መውደቃቸውን ገልጸዋል።

ሁኔታዎች በዚህ ከቀጠሉ በጣና ሃይቅ፣በአባይ ወንዝና በዙሪያው የሚገኙ የቱሪስት መዳረሻ ስፍራዎች ሊጠፉ የሚችሉበት አጋጣሚ ሊፈጠር ይችላል ነው ያሉት።

ከ40 አመታት በላይ በባህር ዳር ኑሮአቸውን ያደረጉ የከተማዋ ነዋሪ ለኢሳት እንደገለጹት መንግስት በአንድ በኩል የአባይ ግድብ መስሪያ እያለ ከሁሉም ኢትዮጵያዊ ገንዘብ ይሰበስባል።

በሌላ በኩል የአባይ ወንዝ በአረም ተወሮ የመድረቅ አደጋ ሲያጋጥመው ብሔራዊ ጥሪ መደረግ ሲገባው በቸልታ መታየቱ አስገራሚ ነው ብለዋል።

የባህር ዳር ከተማ የመንግስት ኮሚኒኬሽን ቢሮ ሃላፊ አቶ በሰላም ይመኑ ከጣና ሃይቅ ባለፈ ወደ አባይ ወንዝም የእምቦጭ አረም መስፋፋት እያሳየ መሆኑን በመጥቀስ አደጋውን ለመከላከል የፌደራል መንግስት የሚጠበቅበትን ያህል አልሰራም በማለት ወቀሳ ማቅረባቸው የሚታወስ ነው።