በአርባምንጭ አካባቢ በመንግስት የጸጥታ ሃይሎች ላይ ለተፈጸመው ጥቃት አርበኞች ግንቦት7 ሃላፊነቱን ወሰደ

ግንቦት ፬ (አራት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- አርበኞች ግንቦት 7 ለኢሳት በላከው ወታደራዊ መግለጫ ፣ በደቡብ ኢትዮጵያ ከሚገኘው የአርበኞች ግንቦት 7 ኃይል ውስጥ በአርባ ምንጭ አካባቢ የሚንቀሳቀሰው አንድ ቡድን ከሚያዝያ 29 ቀን እስከ ግንቦት 1 ቀን ባደረገው የመረረ ፍልሚያ ከሃያ በላይ የጠላት ወታደሮችን ገድሎ ከሃምሳ ያላነሱትን ማቁሰሉንና በጦርነቱም ከአርበኞች ግንቦት 7 ወገንም መስዋዕትነት ተከፍሎአል ብሎአል።

“በወጣት አርበኞቻችን ጀግንነት፣ ጽናትና የጉሬላ ጦር ታክቲክ ክህሎት ኮርተናል። ያደረጉት ተጋድሎ ወደፊት ለሚጠብቃቸው ከዚህ የከፋ ትንቅንቅ ይበልጥ የሚያዘጋጃቸው ሲሆን የሕይወት ዋጋ የከፈሉት ሰማዕታት ጓዶቻችን ታሪክ ደግሞ ህያው ሆኖ ይኖራል።” የሚለው መግለጫው፣ የህይወት ወጋ የከፈሉትን ጓዶቹን በአሃዝ አልገለጸም።
“የአርበኞች ግንቦት 7 ደቡብ ግንባር አባላት በተግባር ያስተላለፉት መልዕክት “መሮናል፤ ዝም ብለን እንደ በግ እየተጎተትን አንታሰርም፤ የካድሬዎች የደም ጥም ማርኪያዎች አንሆንም፤ በአገራችንና በሕዝባችን ላይ የሚደርሰውን መከራ እያየን ዝም አንልም፤ ለነፃነታችን መሞት ካለብን፣ ገድለን እንሞታለን !!!” የሚል መሆኑን የሚገልጸው፣ ንቅናቄው “ ይህ ከኮስታራ ሀሞት የወጣ ድምጽ በመላ ኢትዮጵያ የሚገኙ ወገኖቻችን ድምጽ ሊሆን ይገባል።” ብሎአል።
ወታደራዊ መግለጫው አያይዞም “ትግሉን በሰሜን ኢትዮጵያና በድንበር አካባቢ ተወስኖ የማይቀር መሆኑን ይህ የመጀመሪያ ምልክት ነው፤ በሌሎች ቦታዎች ተመሳሳይ ተጋድሎዎች የሚጀመሩበት ጊዜ ሩቅ አይደለም። በመላው ኢትዮጵያ፤ በሰሜን፣ በደቡብ፣ በምስራቅና ምዕራብ፤ በዳርና በመሀል አገር እንዲሁም በከተሞችና በገጠሮች አርበኞች ግንቦት 7 ለነፃነት የሚደረገውን ፍልሚያ ያቀጣጥላል። ይህ የነፃነት ተጋድሎ አንዳንዴ ቦግ፣ ሌላ ጊዜ ደብዘዝ ይል ይሆናል፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ የሥልጣን ባለቤት ሳይሆን ግን አይጠፋም። “ ብሎአል።
የኢትዮጵያ ሕዝብ በተለይም ወጣቶች ራሳቸውን ለመራር ትግል እንዲያዘጋጁ እና በየአካባቢያቸው ያለውን የጠላት ኃይል ፋታ እንዲነሱ አርበኞች ግንቦት 7 ጥሪ አቅርቧል።
ኢሳት በጦርነቱ 20 የመንግስት የጸጥታ ሃይሎች መገደላቸውን መዘገቡ ይታወቃል። መንግስት በበኩሉ ከኤርትራ በተላኩት አማጽያን ላይ እርምጃ መውሰዱንና የተወሱትን መማረኩን ገልጿል።