በእነ አንዷለም አራጌ የክስ መዝገብ በአሸባሪነት ወንጀል ክስ የመሰረተባቸው ላይ ሊሰጥ የነበረውን የጥፋተኝነት አሊያም ከጥፋት ነፃ የመሆን ብይን በተለዋጭ ቀጠሮ አራዘመ

ጥር 4 ቀን 2004 ዓ/ም

ት ዜና:-የአቶ መለስ መንግሥት በእነ አንዷለም አራጌ የክስ መዝገብ በአሸባሪነት ወንጀል ክስ የመሰረተባቸው 24  የፖለቲካ ፓርቲ የአመራር አባላት፣ ጋዜጠኞች እና ነፃ አሳቢ ዜጎች ላይ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ሦስተኛ ወንጀል ችሎት ዛሬ ሊሰጥ የነበረውን የጥፋተኝነት አሊያም ከጥፋት ነፃ የመሆን ብይን ለጥር 14 ቀን 2004 ዓ.ም በጊዜ ተለዋጭ ቀጠሮ አራዘመ፡፡

በዳኛ እንደሻው አዳነ፣ ሙሉጌታ ኪዳኔ እና በሪሁን አራጋው ዛሬ ጠዋት የተሰየመው ሦስተኛ ወንጀል ችሎት መዝገቡ ለዛሬ የተቀጠረው ዐቃቤ- ሕግ ያቀረበውን ማስረጃዎች በማገናዘብ ብይን ለመስጠት እንደነበር አውስቷል፡፡

በታህሳስ 9 ቀን 2004 ዓ.ም በነበረው ችሎት ቀርቦ የነበረው የድምጽና የምስል ማስረጃዎች ወደ ጽሑፍ ተገልብጠው እንደቀረቡለት የገለጸው ፍርድ ቤቱ ነገር ግን ከዚያ በኋላ በነበሩ ችሎቶች ላይ የቀረቡ የድምጽና የምስል ማስረጃዎች ወደ ጽሑፍ ተገልብጠው ስላልቀረቡልኝ በእለቱ ብይን ለመስጠት ተቸግሬያለሁ ብሏል፡፡

ፍርድ ቤቱ ለጥር 14 ቀን 2004 ዓ.ም ጊዜ ቀጠሮን ማራዘሙን ገልፆ ከቀኑ ቀደም ብሎ ማስረጃዎች ወደ ጽሑፍ ተገልብጠው በጽ/ቤት በኩል ይቅረብልኝ ሲል ትዕዛዝ አስተላልፏል፡፡

የፌዴራል ዐቃቤ- ሕግ በእነ አንዷለም አራጌ የክስ መዝገብ በሽብርተኝነት ወንጀል ከሷቸው ሀገር ውስጥ በማረሚያ ቤት ሆነው ፍርዳቸውን በሚጠባበቁ 8 የፖለቲካ ፓርቲ የአመራር አባላትና ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እና  16 በውጭ አገራት የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፣ ጋዜጠኞችና ነፃ አሳቢ ዜጎች ላይ በሦስት የተከፈሉ የሰው ማስረጃዎችን ያቀረበባቸው ሲሆን የመጀመሪያዎቹ የተጠርጣሪ ግለሰቦች ቤት ሲበረበር ታዛቢ የነበሩ ምስክሮች፣ በሁለተኝነት ምስክርነት የቀረቡት በተዘዋዋሪ በድርጊቱ ተሳታፊ የነበሩ የተባሉ በኮምፒውተር ጽሑፍ ትየባ፣ በፎቶ ኮፒ ማባዣ ሥራ የተሰማሩና በህገወጥ የገንዘብ ዝውውር ብር ተቀባብለናል ያሉ ግለሰቦች ሲሆኑ በሦስተኝነት በቀጥታ የወንጀሉ ተሳታፊ የነበሩ የተባሉት የመኢዴፓ ፓርቲ ዋና ጸሐፊ አቶ ዘመኑ ሞላ፣ የአንድነት ፓርቲ አባል የነበረው አሳምነው ብርሃኑ እና ሌሎችም ከማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ በቁም እስረኝነት ተፈተው በጓዶቻቸው ላይ እንዲመሰክሩ የተደረጉበት መሆኑን መዘገባችን ይታወሳል፡፡