ታጋይ አበበ ካሴ ጨለማ ቤት መክረሙ ታወቀ

ሐምሌ ፭ ( አምስት ) ቀን ፳፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በአርበኞች ግንቦት7 በሽብር ወንጀል ተከሶ በእስር ላይ የሚገኘው ታጋይ አበበ ካሴ ፣ በእስር ቤት የተሰፋለትን ዩኒፎርም አልለብስም በማለቱ ጨለማ ቤት ውስጥ ታስሮ መክረሙ ታውቋል። አበበ ዩኒፎረም እንዲለብስ ሲጠየቅ “ ጥሩ ጊዜ ላይ ነው ያሰፋችሁት እናንተው ትለብሱታላችሁ፣ እኔ አልለብስም” በማለቱ የተበሳጩት ፖሊሶች፡ ለወራት በጨለማ ቤት ውስጥ አስገብተው ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት ፈጽመውበታል። አበበ በቅርቡ ከጨለማ ቤት ወጥቶ ፖሊሶች ጥበቃ ከሚያደርጉበት ማማ ስር ብርድና ሙቀት እየተፈራረቀበት ውሎና አዳሩን እንዲያሳልፍ እየተገደደ ሲሆን፣ ዩኒፎርም አልለብስም በሚለው አቋሙ እንደጸና ነው።
ታጋይ አበበ በተያዘበት ወቅት በማእከላዊ እስር ቤት የሁሉም ጣቶቹ ጥፍሮች ተነቅለው፣ በዘር ፍሬው እና በመላ አካላቱ ላይ ከፍተኛ ድብደባ ተፈጽሞበት መረጃ ለማውጣት ፈቃደኛ ሳይሆን ቀርቶ በመጨረሻ ቂሊንጦ እስር ቤት ከተወረወረ በሁዋላ፣ የደረሰበትን ችግር ሁሉ ዘርዝሮ በመጻፍ ለመገናኛ ብዙሃን በድብቅ እንዲደርስ አድርጎ ነበር።
ከሁለት አመት በፊት ፍርድ ቤት ቀርቦም በእስር ቤት ውስጥ ስለሚፈጸምበት በደል ሲናገር፣ ‹‹ማረሚያ ቤቱ እራሱ ቀበቶ ይሸጣል ግን ቀበቶ ይከለክላል፡፡ ለምን ብለን ስንከለክል ሱሪያችሁን መፍታታችሁን እንድታውቁት ይለናል፡፡ በተለይ እኔ በማንነቴ ላይ ያነጣጠረ ጥቃት እየተፈፀመብኝ ነው›› ብሎ ነበር።
ታጋይ አበበ ዳኞችን ‹‹እናንተ ግዴታችሁን ተወጡ፤ ስለ ስርዓቱ ብዙም ነገር አልልም፤ በእርግጠኝነት ስርዓቱ ይወድቃል›› ማለቱ ይታወሳል።
በመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ታስረው የሚገኙትና በድብደባ ብዛት እግሮቻቸው ሽባ የሆኑባቸው ኮሎኔል ደምሰው አንተነህ ከዞን 4 እስር ቤት ታንከር ወደ ሚባለው ቦታ መዛወራቸው ታውቋል። ኮሎኔል ደምሰው ታንከር ወደሚባለው ቦታ የተዛወሩት በእስር ላይ ከሚገኙት የቀድሞው የደህንነት ሹምና የህወሃት ታጋይ አቶ ወልደስላሴ ወልደሚካኤል ጋር በመጋጨታቸው ነው። ኮ/ል ደምስው የደህንነት ሹሙን “ አንተ እጅ ላይ የብዙ ሰዎች ደም አለ” ብለው እንደተናገሩዋቸው ታውቋል። በሙስና ተከሰው 10 ዓመት ተፈርዶባቸው በእስር ላይ የሚገኙት የቀድሞው የአገር ውስጥ የደህንነት ሃላፊ አቶ ወልደስላሴ ፣ በእስር ቤት የምክር አገልግሎት ይሰጣሉ በሚል ቢሮ ተሰጥቷቸው፣ ሌሎችን እስረኞች እያስፈራሩ ነው።