ፕሬዝዳንት ኢሳያስ ነገ ወደ አዲስ አበባ ሊሄዱ ነው

(ኢሳት ዲሲ–ሐምሌ 6/2010) ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቄ ነገ አዲስ አበባ እንደሚገቡ መንግስት ይፋ አደረገ።

የአዲስ አበባና የአካባቢዋ ነዋሪዎች ለኤርትራው መሪ አቀባበል እንዲያደርጉላቸውም የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ጥሪ አቅርቧል።

የኤርትራው ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቄ ከቅዳሜ ሐምሌ 7/2008 ጀምሮ እስከ ሰኞ ሐምሌ 9/2010 ለሶስት ቀናት በአዲስ አበባ ቆይታ እንደሚያደርጉም ከወጣው መርሃ ግብር መረዳት ተችሏል።

ፕሬዝዳንት ኢሳያስ የኢትዮጵያና የኤርትራ ጦርነት ከፈነዳበት ግዜ ጀምሮ እንዲሁም ከዚያ ጥቂት አመታት ቀደም ብሎ ወደ ኢትዮጵያ ሳይጓዙ ቆይተዋል።

በአንዳንድ መረጃዎች ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቄ ወደ ኢትዮጵያ የሚያደርጉት ይህ ጉዞ ከሩብ ክፍለ ዘመን ማለትም ከ25 አመታት በኋላ የመጀመሪያው ይሆናል።

ሕዝብ አደባባይ ወጥቶ ሲቀበላቸውም የአሁኑ የመጀመሪያው እንደሚሆንም ተመልክቷል።

ፕሬዝዳንቱ በጉዟቸው ወደ ሃዋሳ እንደሚያቀኑና በሚሊኒየም አዳራሽም ለእሳቸው በተዘጋጀው መድረክ ላይ ተገኝተው ንግግር ያደርጋሉ ተብሏል።

ፕሬዝዳንት ኢሳያስ በተገኙበትም የኤርትራ ኤምባሲ እሁድ በአዲስ አበባ ከ20 አመት በኋላ ይከፈታል ተብሎ እንደሚጠበቅ የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።