ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የ2019 የዩኔስኮ ተሸላሚ ሆኑ

(ኢሳት ዲሲ–ሚያዚያ 24/2011)ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የ2019 የዩኔስኮ የሰላም ሽልማት ተሸላሚ ሆኑ።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአፍሪካ ቀንድ በተለይም በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል የሰላም ስምምነት እንዲደረስ ባደረጉት አስተዋጽኦ ለሽልማት መብቃታቸውን የመንግስታቱ ድርጅት የትምህርት፣የሳይንስና የባህል ተቋም ዩኔስኮ ይፋ አድርጓል።

በቀድሞ የአይቬሪኮስት ፕሬዝዳንት ፌሊኒክስ ሃፌፍ- ቦኒይ ስም የሚጠራውን የዩኔስኮ የሰላም ሽልማት የተቀዳጁት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በሀገር ውስጥ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ማሻሻያዎች ለመውሰድ በጀመሩት ጥረትም አድናቆትን እንዳገኙ ተመልክቷል።

ባለፈው ሰኞ በፓሪስ የዩኔስኮ የሰላም ሽልማት ሰጪ ኮሚቴ አባላት የዘንድሮውን ተሸላሚ ለመምረጥ ተሰይመዋል።

የቀድሞ የላይቤሪያ ፕሬዝዳንት ኤለን ጆንሰን ሴርሌፍ፣ የቀድሞ የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ፍራንሷ ሆላንዴ፣ የጆርዳን ልዕልት ሱማያ ቢንት ሀሰን፣ የአይ ኤም ኤፍ የቀድሞ ዳይሬክተር ጄነራል ሚሼል ካምዴሰስ የኮሚቴው አባላት ናቸው።

በቀድሞ የአይቬሪኮስት ፕሬዝዳንት በነበሩት ፌሊክስ ሃፌየት ቦኒየ የተሰየመው የመንግስታቱ ድርጅት የትምህርት የሳይንስና ባህል ተቋም ዩኔስኮ የሰላም ሽልማት ለሰላምና ለዲሞክራሲ መጎልበት አስተዋጽኦ ለሚያደርጉ ሰዎች የሚሰጥ ሲሆን የዘንድሮው ሽልማት ለኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ እንዲሆኑ ወስኗል።

የኮሚቴው አባላት በሰጡት ውሳኔ መሰረት ዶክተር አብይ 30ኛው የሰላም ተሸላሚ ሆነዋል።

ተቋሙ ይህን ክብር ለኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር የሰጠው በአፍሪካ ቀንድ የሰላም አየር እንዲነፍስ ባደረጉት አስተዋጽኦ መሆኑን አስታውቋል።

በተለይም ለ20 ዓመታት የዘለቀውን የኢትዮጵያና የኤርትራ ፍጥጫ እንዲቆም ታሪካዊ የተባለ የሰላም ስምምነት እንዲደርግ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የተጫወቱት ሚና ተጠቅሷል።

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የትምህርት የሳይንስና የባህል ተቋም ዩኔስኮ ዳይሬክተር ኦደሪ አዞውላይ በአሁኑ ሰዓት በኢትዮጵያ በጉብኝት ላይ ሲሆኑ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድን አግኝተው የእንኳን ደስ ያልዎት መልዕክት እንደሚያስተላልፉ ዘገባዎች ያመለክታሉ።

የፌሊክስ ሃፌየት ቦኒየ የሰላም ሽልማት የተቋቋመው በ1989 እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ሲሆን ከ120 በላይ የተባበሩት መንግስታት አባል ሀገራት ድጋፍ ሰጥተው በመካሄድ ላይ ያለ ሽልማት መሆኑንም ለማወቅ ተችሏል።

ሽልማቱ ዓለም አቀፍ ግጭቶችን በመፍታት፣ የውይይትን እና ድርድርን ሚና በማጉላትና በመቻቻል፣ በእኩልነትና በመግባባት ሰላም እንዲሰፍን አስተዋፅኦ ላደረጉ ግለሰቦች ተቋማት በየዓመቱ እንዲሰጥም ሀገራቱ ተስማምተዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በቅርቡ ለንባብ በበቃው ታይም መጽሄት ከዓለማችን ተጽዕኖ ፈጣሪ በመባል ከተመረጡ ታላላቅ ሰዎች አንዱ መሆናቸው የሚታወስ ነው።

ለውጥ በሀገራቸው እንዲመጣ በማድረግ የሚጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ አሁን ላይ ሀገሪቱን እያሰጋት ያለው የፖለቲካና የኢኮኖሚ ቀውስ የማሻሻያ ፕሮግራማቸው ላይ ከፍተኛ ችግር መፈጠሩን ዘገባዎች ያመለክታሉ።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በተለይ በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል የሰላም ስምምነት እንዲደረስ ላደረጉት አስተዋጽኦ የኖቤል የሰላም ሽልማት እንዲያገኙ ግፊት እየተደረገ ሲሆን መቀመጫውን ኖርዌይ ያደረገው የኖቤል ሽልማት ድርጅት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በእጩነት እንዲቀርቡ የሚጠይቀው የህዝብ ጥቆማ እንደደረሰው ማስታወቁ የሚታወስ ነው።