ደቡብ ሱዳን በእርስ በርስ ግጭት እየታመሰች ነው

(ዘጠኝ)ቀን ፳፻፮ /  ኢሳት ዜና :-በፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር እና በቀድሞው ምክትላቸው ሪክ ማቻር መካከል የተነሳው ውዝግብ የዲንቃና የኑዌር ጎሳዎችን እርስ በርስ እንዲዋጉ እያደረጋቸው መምጣቱን ዘገባዎች ያመለክታሉ።

የሪክ ማቻር ደጋፊዎች ጆንግሌ አካባቢ የሚገኙ የተለያዩ ቦታዎችን መቆጣጠራቸው ተሰምቷል። ምንም እንኳ የአገሪቱ መሪ መፈንቅለ መንግስቱን ማክሸፋቸውን ቢናገሩም፣ በሌሎች አገሪቱ ክፍሎች አሁንም ውጊያዎች እየተካሄዱ ነው። ከስልጣን የተባረሩት ሪካ ማቻር ፕሬዚዳንት ሳል ቫኪር ስልጣን እንዲለቁ ጠይቀዋል።

የተባበሩት መንግስታት ድርጅትና ሌሎች መንግስታት ሁለቱ ባለስልጣኖች ቁጭ ብለው እንዲወያዩ ጠይቀዋል። እስካሁን ባለው መረጃ ከ500 ያላነሱ ሰዎች ተገድለዋል። በደቡብ ሱዳን ከ50 ሺ ያላነሱ ኢትዮጵያውያን በተለያዩ ስራዎች ተሰማርተው ይገኛሉ።