የ6 የፖለቲካ ፓርቲዎች ጥምረት ቡድን ግብረ-ሃይል በማቋቋም እየሰራ መሆኑን ገለጸ

(ኢሳት ዲሲ–መጋቢት 19/2011) የ6 የፖለቲካ ፓርቲዎች ጥምረት ቡድን የፓርቲዎችን አባላት ውህደትና የአዲሱን አገር አቀፍ ፓርቲ ምስረታ ሂደት መርኃ-ግብር ለማውጣት ግብረ-ሃይል በማቋቋም እየሰራ እንደሚገኝ ገለጸ፡፡

ጥምረት የፈጠሩት ፓርቲዎቹ ኢዴፓ፣ ሰማያዊ፣ መኢአድ፣ የጋምቤላ ክልላዊ ንቅናቄ፣ አርበኞች ግንቦት 7ና የቀድሞ አንድነት ፓርቲ አመራርና አባላት ናቸው፡፡

ስድስቱ የፖለቲካ ፓርቲዎች በኢትዮጵያ ማህበራዊ ፍትህን የሚያሰፍንና ዜግነትን መሰረት ያደረገ የፖለቲካ ፕሮግራም እንዲሁም የምርጫ ወረዳን መሰረት አድርጎ የሚዋቀር  አደረጃጀት ያለው ፓርቲ ለመመስረት ማቀዳቸውን መግለጻቸው ይታወሳል።

በዚህም መሰረት ፓርቲዎቹ የአባላት ውህደትና የአዲሱን ፓርቲ ምስረታ መርሃ-ግብር አውጥተዋል፡፡

ስልጠናና የፖሊሲ ሰነዶች የሚያዘጋጅ የምሁራን ስብስብ፣ የአባላትን መረጃ የሚያዘጋጅና የሚያዋህድ፣ የፋይናንስ ጉባኤ ዝግጅት እንዲሁም የህዝብ ግንኙነት ግብረ-ሃይል ማቋቋማቸውንም ጥምረቱ አስታውቋል፡፡

ፓርቲዎቹ ግንቦት 1 እና 2 አዲሱን የፖለቲካ ፓርቲ መስራች ጉባኤ ፣ የፓርቲውን ፕሮግራም፣ ስያሜና አርማ ያፀድቃሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡