የፌደራል ፖሊሶች በሳውድ አረቢያ የሚፈጸመውን ግፍ ለመቃወም አደባባይ በወጡ ኢትዮጵያውያን ላይ ጥቃት ሰነዘሩ

ህዳር (ስድስት)ቀን ፳፻፮ / ኢሳት ዜና :-በሳውድ አረቢያ በኢትዮጵያውያን ላይ እየተፈጸመ ያለው ግፍ ተባብሶ በቀጠለበት በዚህ ወቅት፣ የሳውዲን መንግስት ለመቃወም በሳውድ አረቢያ ኢምባሲ ፊት ለፊት ተቃውሞዋቸውን ለመግለጽ የወጡ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች በፌደራል ፖሊሶች ተደብድበዋል።

ከ100 በላይ ሰዎች ታስረው የነበረ ሲሆን እስከ ምሽት ድረስ 40 የሚሆኑት ተለቀዋል። ሰልፉን ያዘጋጀው የሰማያዊ ፓርቲ 15 የአመራር አካላትም በእስር ላይ እንደሚገኙና ይህን ዜና እስካጠናከርንበት ጊዜ ድረስ አለመፈታታቸው ታውቋል።

የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ የሆነው ወጣት ብርሀኑ ተክለያሬድ እስር ቤት ውስጥ ሆኖ በድብቅ በስልክ እንደተናገረው የድርጅቱን ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነትንና ምክትላቸው አቶ ስለሺ ፈይሳን ጨምሮ 15 አመራሮች ጃንሜዳ በሚገኝ እስር ቤት ውስጥ ይገኛሉ። ወጣት ጥላየ ታረቀኝ ታስሮና ድብደባ ተፈጽሞበት ከተለቀቁት መካከል አንዱ ሲሆን ፣ የኢትዮጵያን መንግስት ድርጊት ለመግለጽ እንደሚቸገር ገልጿል።

ሌሎች አስተያየት ሰጪዎችም በመንግስት ድርጊት አገር አልባነት እንደተሰማቸው  ይናገራሉ

ሰማያዊ ፓርቲ ከጥቃቱ በሁዋላ ባወጣው መግለጫ ” የኢትዮጵያ መንግስት ከሳውዲ አረቢያ መንግስት ጎን በመቆም ዋና ተባባሪ መሆኑን በዛሬው እለት አስመስክሯል ብሎአል።

የመንግስት ፖሊሶች የራሳቸውን ዜጋ በመደብደብና በማሰቃየት ብሎም በማሰር በሳውዲ በሚገኙ ኢትዮጵያዊ ወገኖች ላይ የተፈጸመውን በደል ሀገር ውስጥ በሚገኙ ንጹሀን ወገኖቻቸው ላይ ደግመውታል ብሎአል።

በውሸት ዲሞክራሲ ስም የተደበቀው አምባገን መንግስት ህዝብን ለማሸማቀቅ የወሰደውን እርምጃ በመቋቋም የኢትዮጵያ ህዝብ አያት ቅድመ አያቶቻችን የሰጡንን አደራ በመቀበል ያስረከቡትን ክብርና ማንነት ለማስመለስ ወደ ሁዋላ እንደማንል እርገኛ መሆናችንን እንገልጻለን ብሎአል።

የመንግስት ቃል አቀባይ የሆኑት ሽመልስ ከማል ለአልጀዚራ  ሰልፈኞቹ የተከለከሉት ባልተፈቀደ ሰልፍ ላይ በመገኘታቸውና ኢትዮጵያን ህዝብ በጸረ-አረብ ስሜት በማነሳሳታቸው ነው ብለዋል።