የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር በኢቦላ በሽታ የተጠቁ ሶስት የምዕራብ አፍሪካ አገራትን ለመደገፍ ባለሙያዎችን በቀጣይ ሳምንት ለመላክ መዘጋጀቱን አስታወቀ፡፡

ኀዳር ፲፭(አስራ አምስት) ቀን ፳፻፯ / ኢሳት ዜና :-በበጎፈቃደኝነት ወደምዕራብ አፍሪካ ሀገራት ሄደው ለመስራት ካመለከቱ ባለሙያዎች መካከል የተመረጡ መሆናቸውን ሚኒስቴሩ ገልጿል።  ሌሎች ምንጮች ደግሞ አብዛኛዎቹ ባለሙያዎች በመከላከያ የጦር ክፍሎች ውስጥ በሕክምና ሙያ

እያገለገሉ የሚገኙ ዶክተሮች ፣ ነርሶችና የጤና መኮንኖች ናቸው ይላሉ። ወዶ ዘማች ናቸው የተባሉትና 210 የሚደርሱት እነዚሁን ባለሙያዎች የፊታችን ሰኞ ህዳር 22 ቀን 2007 ዓ.ም ወደሶስት የምዕራብ አፍሪካ ሀገራት እንደሚላኩ ታውቓል።

የአፍሪካ ህብረት ኮምሽን ሊቀመንበር ዶ/ር ዲላሚኒ ዙማ በቅርቡ የአፍሪካ መንግስታት ኢቦላ ወደተንሰራፋባቸው ሀገራት ባለሙያዎችን በመላ እንዲተባበሩ ላቀረቡት ተማጽኖ በፍጥነት መልስ የሰጠው የኢህአዴግ መንግስት ብቻ ነው፡፡

አንዳንድ ሀገራት ኢቦላ ወደሀገራቸው እንዳይገባ የአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅነትን ኃላፊነት ሁሉ አስከመሰረዝ የደረሰ ከባድ ጥንቃቄ በሚያደርጉበት በዚህ ወቅት ገዢው ፓርቲ ለተራ ፕሮፖጋንዳ ፍጆታ ሲል ባለሙያዎችን ወደምዕራብ አፍርካ ሀገራት ለመላክ የወሰነበት ሁኔታ የሕዝብንና የሀገርን ጥቅም ያላገናዘበ ነው በሚል ሲተች ቆይቷል።