የጋምቤላ ጭፍጨፋ 9ኛ አመት ታስቦ ዋለ

 

426 የአኝዋክ ብሄረሰብ ተወላጆች የተገደሉበት 9ኛው አመት የጋምቤላ ጭፍጨፋ ዛሬ በመላው ዓለም ታስቦ ውሏል።

በተለይም የአኝዋክ ብሄረሰብ ተወላጆች በብዛት በሚገኙበት የሜኒሶታ ግዛት መታሰቢያው በሀዘን ድባብ እየተደረገ መሆኑን ዶ/ር ማኝ ኛንግ ለኢሳት ገልጸዋል።

ከ9 አመት በፊት፤ በታህሳስ 1996 ዓ.ም. በአኝዋክ ብሄረሰብ አባላት እንደተገደሉ የሚጠረጠሩ ስምንት የመሀል አገር ሰዎችን ወይም ደገኞችን ሞት ለመበቀል በሚል ሰበብ፤ የመንግስት ወታደሮች የተማሩ አኝዋክ ብሄረሰብ ተወላጆችን ስምዝርዝር በመያዝ በጋምቤላ በአንድ ቅዳሜ ብቻ 426 የአኝዋክ ተወላጅ ወጣት ወንዶችን ገድለዋል።

በወቅቱ የተወካዮች ምክር ቤት ያቋቋመው የመርማሪ ኮሚሽን ጉዳዩን አጣርቶ 67 ሰዎች ብቻ መገደላቸውን ቢያምንም፤ የአኝዋክ ፍትህ ምክርቤትን ጨምሮ የተለያዩ ገለልተኛ ወገኖች የተገደለት ሰዎች ቁጥር 400 እንደሚበልጥ አረጋግጠዋል።

ሟቹ ጠ/ሚር አቶ መለስ ዜናዊ ግድያውን የፈጸሙት ሰዎች ለፍርድ እንደሚቀርቡ ቢናገሩም፤ እስካሁን ተይዞ ለፍርድ የቀረበ ሰው እንደሌላ ዶ/ር ማኝ ኛንግ ተናግረዋል።

የጋምቤላው ጭፍጨፋ ጄኖሳይድ ወች የተባለ አለማቀፍ የዘር ማጥፋት ወንጀል ተከላካይ ድርጅት ወደኢትዮጵያ በላከው መርማሪ ቡድን ተጠንቶ፤ የድርጅቱ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ገሪጎሪ ስታንተን ጉዳዩ በአለም አቀፉ ፍርድ ቤት ሊመረመር የሚገባው ለዘር ማጥፋት የቀረበ በሰብአዊነት ላይ የተቃጣ ወንጀል ነው ሲሉ አውግዘዋል።

ከጋምቤላው ጭፍጨፋም በሁዋላ በጋምቤላ በአኝዋክ ብሄረስበ ተወላጆች ላይ የሚደርሰው ጭፍጨፋ እንደቀጠለ ሲሆን፤ ከ1996 ታህሳስ የመጀመሪያ ቅዳሜ በሁዋላ የተገደሉት ሰዎች ቁጥር አንድ ሺህ አምስት መቶ መድረሱን መረጃዎች ያመለክታሉ።