የዜጎች መታፈን ተባብሶ ቀጥሎአል

ሚያዝያ ፭ (አምስት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ካለፉት ሁለት ሳምንታት ጀምሮ አገዛዙን ይቃወሙ ይሆናል ተብለው የሚጠረጠሩ ሰዎች በገፍ እየተያዙ በመታሰር ላይ ሲሆኑ፣ በርካታ ወጣቶችም ከእስር ለማምለጥ መሸሸጋቸውን ለኢሳት እየገለጹ ነው።

በተለያዩ ክልሎች የገዢው ፓርቲ አባል ለመሆን ፈቃደኛ ያልሆኑ ወጣቶች የሚታሰሩት ከምርጫው ጋር በተያያዘ ህዝቡን ለአመጽ ያነሳሳሉ በሚል ነው።

የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት መሪ የነበሩት አቶ ማሙሸት አማረ   ዛሬ ግንቦት5 ረፋዱ ላይ በአዲስ አበባ ፖሊሶች ተይዘው ታስረዋል። አቶ ማሙሸት እጆቻቸው በካቴና ታስረው ፖሊስ ጣቢያ ውስጥ ታይተዋል።

በጎንደር ደግሞ አቶ አዋጁ አቡሃይ አደመ እና አቶ አዳነ ባብል ታደሰ የተባሉት ሁለት ግለሰቦች ጸጥታ ሃይሎች ታፍነው ተወስደዋል።

ሁለቱ ታዋቂ ሰዎች ከዚህ ቀደም በተደጋጋሚ መታሰራቸው ይታወቃሉ። ከ5 ቀናት በፊት ደግሞ ጎንደር ከተማ አራዳ ቅዳሜ ገበያ አካባቢ 10 ሰዎች በፌደራል ፖሊሶች ታፍነው መወሰዳቸውን ምንጮች ገልጸዋል።

በሰሜን ጎንደር አካባቢ የሚታየው ውጥረት መጨመሩን ተከትሎ ስርአቱን እየተዉ በትጥቅ ትግል የሚያምኑ የተቃዋሚ ሃይሎችን የሚቀላቀሉ ወጣቶች ቁጥረም ጨምሯል።