የኮሎኔል ደመቀ የፍርድ ሂደት ወደሚቀጥለው ሳምንት ተዛወረ

(ሃምሌ 22 ፥2008)

የኮሎኔል ደመቀ የፍርድ ቤት ጉዳይ ወደሚቀጥለው ሳምንት መዛወሩ ተገለጸ። የጎንደር ህዝብ በነቂስ በመውጣት ኮሎኔሉ እንዲፈቱ ጠይቋል። ለኢሳት በደረሰ መረጃ የደህንነት መስሪያ ቤቱ ለጎንደር ከፍተኛ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ በመስጠት ጉዳዩ በፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት እንዲታይ ተወስኗል። ዛሬ ኮሎኔሉ ፍርድ ቤት በአካል ያልቀረቡ ሲሆን ምክንያቱ በሚመለከተው አካል ያልተገለጸለት የጎንደር ህዝብ ለሰዓታት በፍርድ ቤቱ ዙሪያ ሆነ ሲጠባበቅ እንደነበረ ለማወቅ ተችሏል። ከጠዋት ጀምሮ ኮሎኔሉ ከሚገኙበት የአንገረብ ወህኒ ቤት አንስቶ እስከከፍተኛው ፍርድ ቤት ድረስ መንገዶች በህዝቡ ተሞልተው እንደነበረና ከቀትር በኋላም በተለይ በከፍተኛው ፍርድ ቤት አካባቢ በብዙ መቶች የሚቆጠሩ ነዋሪዎች ምላሽ ለማግኘት ሲጠባበቁ መዋልቸውን ኢሳት ያነጋገራቸው ሰዎች ገልጸዋል። ኮሎኔሉ በይፋ ክስ እንደቀረበባቸው ሳይገለጽ ለዛሬ በፍርድ ቤት ጉዳያቸው እንደሚታይ መረጃ የደረሰው ህዝብ ከጠዋት ጀምሮ ወደ ከፍተኛው ፍርድ ቤት የተጓዘ ቢሆንም ስለሁኔታው ምላሽ የሚሰጥ የመንግስት አካል አልነበረም።colonel Demeke

ኢሳት ወደ ጎንደር ከፍተኛው ፍርድ ቤት በመደወል ዳኛ ራራ ደሴን ያነጋገረ ሲሆን እሳቸውም ኮሎኔሉ በአካል ፍርድ ቤት አለመቅረባቸውን ጠቅሰው ጉዳዩ በሚቀጥለው ሳምንት እንደሚታይ ገልጸዋል። በሌላ በኩልም ኢሳት በደረሰው መረጃ የኮሎኔል ደመቀ ጉዳይ ወደ ፌደራል እንዲተላለፍና የጎንደር ከፍተኛው ፍርድ ቤት የማየት ስልጣን የለውም በሚል ፋይል ዘግቶ ወደ ፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት አዲስ አበባ እንዲልከው በደህነንት መስሪያ ቤቱ ታዟል። ይህን በተመለከተ ያነጋገርናቸው የሰሜን ጎንደር ዞን ከፍተኛው ፍርድ ቤት ዳኛ ራራ ደሴ ማስተባበልም ማረጋገጥም ሳይችሉ በደፈናው ጉዳዩ በሚቀጥለው ሳምንት ይታያል ብለዋል።

የኢሳት ምንጮች እንደገለጹት በደህንነት መስሪያ ቤቱ በኩል እየተደረገ ባለ ግፊት ኮሎኔል ደመቀን አዲስ አበባ ማዕከላዊ በመውሰድ በህወሀት ደህንነቶች ምርመራ እንዲደረግ ታቅዷል። ከጎንደር ወህኒ ቤት የሚገኙት ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ ለህወሀት ደህንነቶች ተላልፈው ከተሰጡ ለህይወታቸው አስጊ በመሆኑ የጎንደር ህዝብ ነቅቶ እንዲጠብቅ ስማቸውን እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የወልቃይት የአማራ ማንነት ኮሚቴ አንድ አባል ለኢሳት ገልጸዋል። በሌላ በኩል ለፊታችን እሁድ ለተጠራው ህዝባዊ ተቃውሞ ከተላያዩ አከባቢዎች ህዝቡ ወደ ጎንደር ከተማ የገባ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል። ተቃውሞ ሰልፉን በተመለከተ የጎንደር አስተዳደር እስከአሁን እውቅና አልሰጠውም። ህዝብ ግን ዝግጅቱን እያደረገ መሆኑን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።