የኬንያ ፍርድ ቤት 40 ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገራቸው ይመለሱ ሲል ውሳኔ አሳለፈ

(ኢሳት ዜና–መስከረም 15/2010) የኬንያ ፍርድ ቤት ወደ ሀገሪቱ በህገወጥ መንገድ ገብተዋል ያላቸው 40 ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገራቸው ይመለሱ ሲል ውሳኔ አሳለፈ።

ፍርድ ቤቱ ኢትዮጵያውያኑ ወደ ሀገራቸው ከመመለሳቸው በፊትም የአንድ ወር እስራትና እያንዳንዳቸው 20 ሺ ሽልንግ እንዲቀጡም ወስኗል።

አብዛኞቹ እድሜያቸው በ20ዎቹ አጋማሽ ላይ እንደሆነ የተገለጸው ኢትዮጵያውያን ወደ ኬንያ በህገወጥ መንገድ የገቡት ወደ ደቡብ አፍሪካ ለመሸጋገር ነው በሚል ፍርድ ቤቱ ያቀረበባቸውን ክስ አምነዋል።

40ዎቹ ኢትዮጵያውያን የሚከራከርላቸው ወይንም ዜጎቼ ብሎ ስለመብታቸው የሚቆምላቸው መንግስት ባይኖርም ራሳቸው ግን ፍርድ ቤቱ ያሳለፈባቸውን ውሳኔ እንዲቀይርላቸውና ይቅርታ እንዲያደርግላቸው እምባቸውን በማፍሰስ ጠይቀዋል።

ኢትዮጵያውያኑ የተወሰነባቸውን የገንዘብ ቅጣትንም ቢሆን ስራ ስለሌላቸው መክፈል እንደማይችሉ ፍርድ ቤቱን ጠይቀዋል። –ፍርድ ቤቱ ለጥያቄያቸው ምን መልስ እንደሰጠ ባይታወቅም እንኳ።

በፍርድቤቱ የቀረቡት 67 ኢትዮጵያውያን ቢሆኑም 27ቱ ግን ወደ ሀገሪቱ በህገወጥ መንገድ አልገባንም ሱሉ በመከራከራቸው ጉዳያቸው በይደር ተይዟል።

ወደ ሀገሪቱ ሲገቡ ገንዘባቸውንም ሆነ ፓስፖርታቸውን ጨምሮ አጠቃላይ ማስረጃቸውን የፖሊስ ሃላፊዎቹ ወስደውብናል የሚል የመከራከሪያ ነጥብም አቅርበዋል።

ዳኛው የ27ቱ ኢትዮጵያን ጉዳይ እስከሚጣራም በጊጊሪ ፖሊስ ጣቢያ እንዲቆዩ ትእዛዝ ሰጥተዋል።መረጃውን ያገኘንው ከኬንያ የዜና አውታር ነው።