የኦባማ የኢትዮጵያ ጉብኝትን የሚቃወም ሰልፍ ተጠራ

ኢሳት ዜና (ሰኔ 22 2007 ዓም)

በሚቀጥለው ወር በኢትዮጵያ ጉብኝት የሚያደርጉት የአሜሪካ ፕሬዘዳንትን ጉዞን በመቃወም የፊታችን አርብ በዚህ በአሜሪካ ዋሺንግተን ዲሲ ከተማ በሚገኘው “ ሁዋይት ሀውስ ‘’ የተቃውሞ ሰልፍ መጠራቱን አዘጋጆቹ ገለጹ ።

በዋሺንግተን ከተማ ዙሪያ በሚገኘው የወጣቶች ግብረ ሀይል የተዘጋጀው የተቃውሞ ሰልፍ ፕሬዘዳንት ኦባማ የሚያደርጉትን ጉዞ እንዲያስቡበትና እንዲሰርዙት የሚጠይቅ መሆኑ ታውቋል።

ፕሬዘዳንቱ በቀጣዩ ወር በኢትዮጽያ የሚያደርጉት ጉብኝት ይፋ መደረግን ተከትሎ የተለያዩ አለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ተቃውሞ ሲያቀርቡ መቆየታቸው ይታወሳል።
ፕሬዘዳንት ባራክ ኦባማ በኢትዮጵያ የሚኖራቸው ቆይታ የተሳሳተ መልክት እንዲኖር ያደርጋል በማለት ድርጅቶቹ ቅሬታቸውን አቅርበዋል።

ከሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶቹ በተጨማሪም የዋሺንግተን ፖስት ጋዜጣ አቋሙን በሚገልጽበት ርዕሰ-አንቀጽ ፕሬዘዳንቱ ወደ ኢትዮጵያ የሚያደርጉትን ጉዞ ተችቷል።
የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፕሬዘዳንት አባማ በምስራቅ አፍሪካ በሚያደርጉት ጉዞ በአለም አቀፍ የጸጥታና የኢኮኖሚ ጉዳዮች ዙሪያ ምክክር እንደሚያድርጉ ገልጸዋል።
ይሁንና በርካታ አለም አቀፍ ተቋማት ፕሬዘዳንቱ በኢትዮጵያ የሚያደርጉት ቆይታ የተሳሳተ መልክትን ያስተላልፋል በሚል ተቃውሞአቸውን እያቀረቡ ይገኛሉ።

የፊታችን አርብ የተጠራው የተቃውሞ ሰልፍም እነዚህን ጉዳዮች በስፋት እንደሚያንጸባርቅ የሰልፉ አዘጋጆች አስረድተዋል።

ነዋሪነታቸው በዚሁ በዋሺንግተን ዲሲ ከተማና አካባቢዋ የሆኑ ኢትዮጵያውያንም በእለቱ በነቂስ በመውጣት በሰልፉ እንዲገኙ አዘጋጆች ጠይቀዋል።