የኢትዮ-ጅቡቲ የባቡር መንገድ ግንባታ በከፍተኛ ሙስና ስራውን ማጠናቀቅ አልቻለም

ጥቅምት ፯ (ሰባት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የህወሀቱ መስፍን ኢንጂነሪንግ ኩባንያ በሀዲድ አምራችነት የሚሳተፍበት የኢትዮ-ጅቡቲ የባቡር መንገድ ግንባታ በከፍተኛ ሙስና ስራውን ማጠናቀቅ አልቻለም

ከአውሮፓ ኀብረት የ114 ኪሎሜትር የባቡር ሐዲድ በአዲስ መልክ ለመገንባት ለኢትዮጽያ መንግስት የተሰጠው ገንዘብ
በትትክክል ሥራ ላይ አለመዋሉን ከኢትዮ-ጅቡቲ ምድር ባቡር ድርጅት የተገኘ መረጃ አመልክቷል፡፡
ገንዘቡ በዕርዳታ መልክ ከዛሬ አምስት ዓመት በፊት መሰጠቱን ያስታወሱት ምንጮቹ ከ114 ኪሎሜትር ውስጥ እስካሁን
ማጠናቀቅ የተቻለው በድምሩ 17 ኪሎ ሜትር ገደማ ብቻ ነው፡፡ መተሐራ አካባቢ ውሃው ላይ ወደ 7 ኪሎሜትር ገደማ
የባቡር ሐዲድ ኮናስታ በተባለ የጣሊያን ኩባንያ መሰራቱን ያስታወሰው ምንጫችን ፣ ነገር ግን ሥራው በጥራት ባለመጠናቀቁ ሐዲዱ አገልግሎት ሳይሰጥ ወደ ውሃው መስመጡን ተናግረዋል፡፡

ሌላው ከድሬዳዋ እስከ ሸንሌ ያለው 10 ኪሎ ሜትር ገደማ መንገድ ተጠናቋል ተብሎ ከትላንት በስቲያ ሰኞ ዕለት የትራንስፖርት ሚኒስቴር ተወካይ ባሉበት በሸንሌ የምረቃ በዓል መካሄዱ ሰፊውን ሠራተኛ ግራ ያጋባ ክስተተት እንደሆነም ተናግረዋል፡፡
ግንባታው በውሉ መሰረት ካለመካሄዱም በተጨማሪ ለ114 ኪሎሜትር በአውሮፓ ኀብረት ሰዎች ጭምር ተረጋግጦ የተፈቀደ
ገንዘብ ባልታወቀ ሁኔታ ለ17 ኪሎሜትር ወጪ ከመደረጉም ባሻገር ይህንኑ ሥራ ለመረከብ የተደረገው መጣደፍ
በሰራተኛው ዘንድ መደናገር መፍጠሩን አስረድተዋል፡፡
ሥራው እንደተጀመረ ተቆጣጣሪ መሐንዲስ በመሆን በትውልድ ኢትዮጵያዊና በዜግነት ስፔናዊ የሆኑ አቶ አስረስ ኪዳኔ
የተባሉ ባለሙያ ሥራው በጥራት እየተሰራ አለመሆኑን፣የሐዲድ ማምረት ሥራ በዘርፉ ልምድ ለሌለው መስፍን
ኢንጂነሪንግ የተባለው የህወሀት የንግድ ድርጅት መሰጠቱን በመቃወማቸው ምክንያት አለመግባባት ተፈጥሮ
ሥራውን ጥለው ለመውጣት መገደዳቸውን ያስታወሰው የድርጅቱ ምንጭ ፣ በሳቸው እግር ተቆጣጣሪ መሐንዲስ የሆነው ራሱ
ምድር ባቡር ድርጅት መሆኑን ገልጾአል፡፡

በአሁኑ ሰዓት የኢትዮ-ጅቡቲ ምድር ባቡር በኪሳራ ላይ በመሆኑ በኢትዮጵያ በኩል ሰራተኞቹን ብቻ ተቀብሎ
የሚያስተዳድረው የብረታብረት ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሸን የሚባለው ተቋም ነው፡፡

የኢትዮጵያ አዲሱ ጠ/ሚኒስትር አቶ ኃይለማርም ደሳለኝ ትላንት ፓርላማ ተገኝተው የፕሬዚዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ
ንግግር ተንተርሰው የመንግስታቸውን አቋም በገለጹበት ንግግራቸው አጓጊ ካሏቸው ፕሮጀክቶች ባቡር አንዱ ሲሆን
አፈጻጸሙም በመልካም ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ መግለጻቸው ይታወሳል።

መንግስት በአምስት አመቱ የልማት እቅድ ውስጥ ሊሰራቸው ከሚያስባቸው የሀዲድ እና የመንገድ ግንባታዎች ውስጥ የህወሀት ኩባንያዎች በስፋት እየተሳተፉ መሆኑ ይታወቃል። ብሉምበርግ በቅርቡ እንደዘገበው ሌላው የህወሀት ኩባንያ የሆነው ሱር ኮንስትራክሽን ባለፈው አመት ከ200 ሚሊዮን ብር በላይ ትርፍ ማግኘቱን መግለጹ ይታወሳል።